ለወራት የሚያገለግለው የHIV ተሐዋሲ መድኃኒት
ማክሰኞ፣ ግንቦት 18 2018
ኢ የኤች አይ ቪ ተሐዋሲን ለመከላከል ያስችላል የተባለ መድኃኒትን ኢትዮጵያ በቅርቡ ለማስገባት እየሠራች መሆኗን የጤና ሚኒስቴር ይፋ ካደረገ ሰነበተ። በመርፌ መልክ በዓመት ሁለት ጊዜ እንደሚሰጥ የተገለጸውን ይህን መድኃኒት የሚወስዱ ደግሞ ተሐዋሲው በደማቸው ውስጥ የማይገኝ፤ ሆኖም ግን ለተሐዋሲው ተጋላጭ ሊሆኑ የሚችሉ የኅብረሰብ ክፍሎች ናቸው። ቀደም ሲልም በእንክብልና በመርፌ መልክ የሚሰጡ የኤች አይቪ መድኃኒቶች እንዳሉ ይታወቃል፤ ሌና-ካፓቨር የተሰኘው ይህ መድኃኒት በምን ይለያል የሚለውን ለዶቼ ቬለ ያብራሩት በኢትዮጵያ ጤና ሚኒስቴር የኤች.አይ.ቪ ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር መሪ ሥራ አስከያጅ አቶ ፍቃዱ ያደታ፤ እንደሚሉት ከዚህ ቀደም የነበረው በዓመት አራት ጊዜ የሚሰጥ መሆኑን አስረድተዋል።
ተጋላጭ ካሏቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች ሴተኛ አዳሪዎችን በዋናነትየጠቀሱት ባለሥልጣኑ፤ ከባል ወይም ከሚስት አንዳቸው ተሐዋሲው በደማቸው መኖሩ ተረጋግጦ ላልተያዘው አካል ተሐዋሲው እንዳይተላለፍ ለማድረግ እንደሚረዳም ነው የተናገሩት። በጉዳዩ ላይ ሙያዊ ማብራሪያ የጠየቅናቸው የውስጥ ደዌ እና ተላላፊ በሽታዎች ተባባሪ ፕሮፌሰር ዶክተር ወንድወሰን አሞኘም ይህንኑ ያረጋግጣሉ።
ስለመድኃኒቱ ምንነት
ብዙዎች መድኃኒት የሚለውን ጽንሰ ሀሳብ ከፈዋሽነት ጋር በማዛመድ ስለሚገነዘቡ ስለ ኤች አይቪ መድኃኒቶች ሲነገር ተሐዋሲውን የሚያጠፋ እንደሆነ አድርገው የመውሰድ ነገር እንዳለ በተለያዩ አጋጣሚዎች በዘርፉ ላይ የሚሠሩ ወገኖች ያነሳሉ። የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ባለፈው መስከረም ወር ወደ ሀገር እንደሚያስገባ የገለጸው በመርፌ የሚሰጠው የኤች አይ ቪ መድኃኒትም ተመሳሳይ ግንዛቤ እንዳያስይዝ ስጋታቸውን ይገልጻሉ። በኢትዮጵያ ጤና ሚኒስቴር የኤች.አይ.ቪ ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር መሪ ሥራ አስከያጅ አቶ ፍቃዱ ግን የተባለው መድኃኒት ለኤች አይቪ ያድናል የሚባለው ስህተት መሆኑን በአጽንኦት ገልጸዋል።
ኤችአይቪ ገና ፈዋሽ መድኃኒት አልተገኘለትም
ዶክተር ወንድወሰንም በግልጽ መነገር አለበት ያሉት ምንም እንኳን በምርምሩ ዘርፍ ብዙ ሥራዎች ለመሠራት ቢሞከርም ለኤች አይቪ ተሐዋሲ ገና የሚያድነው ወይም የሚያጠፋው መድኃኒት አልተገኘም የሚለው ነው።
ለኤች አይቪ ተገኙ የሚባሉ መድኃኒቶችን በሚመለከት በተለይ ክትባት የሚለው አገላለጽ፤ ተገቢ እንዳልሆነ የተናገሩት የውስጥ ደዌ እና ተላላፊ በሽታዎች ተባባሪ ፕሮፌሰር ለኤች አይቪ ያለው በመርፌ እንደኢንሱልን ሆድ ላይ የሚሰጥ የተሐዋሲውን አቅም የሚያደክም መድኃኒት መሆኑን አብራርተዋል።
የቅስቀሳ መቀዛቀዝ
በአሁኑ ወቅት የኤች አይቪ ተሐዋሲ ስርጭት እንዲገታ ይደረጉ የነበሩ ቅስቀሳዎችና ልዩ ልዩ ትኩረትን የሚስቡ እንቅስቃሴዎች መቀዛቀዝ የዘመኑ ወጣት ትውልድ ይህ ተሐዋሲ ያደረሰውና እያደረሰ ያለው ጉዳትን እንዳይገነዘብ እንዳደረገው ነው ዶክተር ወንድወሰን ያመለከቱት። ለዚህ ደሞ ዋነኛው ምክንያት አንድም ለዘርፉ ይደረግ የነበረው የበጀት ድጋፍ መስተጓጎል እና የሚወሰዱ መድኃኒቶች በገፍ ይከሰት የነበረው ሞት ድግግሞሹ በመቀነሱ መሆኑን ያነሳሉ።
ዶክተር ወንድወሰን እንደተናገሩት ዛሬም የኤች አይቪ ተሐዋሲ ስርጭት አልተቆረጠም። ከገጠር ይልቅ በንጽጽርም በተለይ ደግሞ በከተሞች አካባቢ መዛመቱ እንደሚበዛም መረጃዎችን ዋቢ በማድረግ ጠቁመዋል። በይበልጥ ተጋላጭ የሆኑት ደግሞ ከአስራዎቹ እስከ አርባዎቹ የዕድሜ ክልል የሚገኙ የኅብረተሰብ ክፍሎች መሆናቸውንም አመልክተዋል።
መድኃኒቶቹን ጥቅም ላይ መዋል ተከትሎም በአሁኑ ጊዜ ሰዎች ኤች አይቪ ተሐዋሲ በደማቸው ውስጥ እያለም ጤናማ እንደሆነው ረጅም ዕድሜ መኖር መቻላቸውንም አንስተዋል። በዚህ ምክንያትም አንዳንዶች የተሐዋሲውን መኖር ችላ ብለው እንዲዘናጉ ማድረጉን በማመላከት የተቀዛቀዘውን የግንዛቤ ማስጨበጫ እንቅስቃሴ በተቀናጀ መልኩ መሥራት እንደሚያስፈልግ ተናግረዋል። ከዚህም ሌላ መድኃኒቶች ኢትዮጵያ ውስጥ መኖራቸውን የገለጹት ዶክተር ወንድወሰን ለሚፈልጓቸው ወገኖች የማዳረሱ ሥራ ግን ገና ይቀረዋል ነው የሚሉት።
ኤችአይቪ በደማቸው ውስጥ ለሚገኝ ወገኖች የተሐዋሲውን መጠንና የመዛመት አቅም የሚገቱ መድኃኒቶች ዛሬ በእርግጥም የሞት ወሬን መቀነስ አስችለዋል። ተሀዋሲው ግን አለ፤ እየተዛመተ ነው ዛሬም ማስተዋል፤ ጥንቃቄን ይጠይቃል። ለሰጡን ማብራሪያ ባለሙያዎቹን እናመሰግናለን።
ሸዋዬ ለገሠ
አዜብ ታደሰ