ሥጋት ያጫረው አዲሱ የኤቦላ ተሐዋሲ
ቅዳሜ፣ ሰኔ 6 2018
የአፍሪቃ የበሽታ መቆጣጠሪያ እና መከላከያ ማእከላት (CDC ) እጅግ እየተስፋፋ በመጣው ኢቦላ ተሐዋሲ ወጣቶች በዋናነት እየተጠቁ መኾናቸውን ዐሳውቋል ። በተሐዋሲው የተነሳ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥርም ከፍ ማለቱ ተነግሯል ። ተቋሙ ይፋ እንዳደረገው ከኾነ፦ እስከ ሐሙስ ዕለት ከኢቦላ ተሐዋሲ ጋር በተገናኘ የተመዘገቡ ሰዎች ቁጥር 635 ደርሷል ። የሟቾች ቁጥር ደግሞ በኮንጎ እና ኡጋንዳ ውስጥ ወደ 127 ከፍ ብሏል ። ይህ ቁጥር ዘገባው ይፋ ከኾነበት ሐሙስ በኋላ ባሉት ሁለት ቀናት ለውጥ ሊኖረው ይችላል ።
በተጠቀሱት የአፍሪቃ አገራት የተቀሰቀሰው የኢቦላ ተሐዋሲ ብዙም ባልተለመደው የቡንዲቡግዮ ተሐዋሲ የተነሳ መኾኑም ተዘግቧል ። ይህን ተሐዋሲ ለመዋጋት ከቤተ ሙኩራ አልፎ በሰዎች ላይ ሊሞከር ከተዘጋጀው በስተቀር በይፋ ተግባራዊ የኾነ የተረጋገጠ ክትባት አለያም ሕክምና የለውም ።
የአፍሪቃ የበሽታ መቆጣጠሪያ እና መከላከያ ማእከላት ዋና ኃላፊ ዶ/ር ዦን ካሴያ እንደሚሉት፦ የቡንዲቡግዮ ተሐዋሲ ኢቦላ በሌላ ስሙ ከሚታወቅበት «የዛየር ተሐዋሲ» አይነት በተለየ መልኩ በ16 ቦታዎች ላይ ዳግም ለመቀስቀሱ ሰበብ ነው ።
«እስካሁን ድረስ አንድም የአፍሪቃ አገር ለቡንዲቡግዮ ተሐዋሲ ማከሚያ በሙከራ ላይ ያለ መድኃኒት የሚጠቀም የለም ። ኾኖም ግን ያዘጋጀነው ክትባት፣ ያዘጋጀናቸው እጩ አካሚዎች አሉን ። በሰዎች ላይ የሚደረግ ሙከራ መጀመር፤ ለአገራትም በሰዎች ላይ ለሚደረጉ ሙከራዎች መስማማት ያስፈልገናል ። »
አዲሱ አይነት የኢቦላ ተሐዋሲ በፍጥነት መስፋፋቱን ለመግታት በሚደረገው ርብርብ ብርቱ ተግዳሮት የፈጠሩ ጉዳዮች አልታጡም ። ከነዚያ መካከል በተቆጡ የማኅበረሰብ አባላት የጤና አገልግሎት ሰጪዎች ላይ የሚሰነዘሩ ጥቃቶች በዋናነት ይጠቀሳል ። አንዳንድ የአካባቢው ማኅበረሰብም ተሐዋሲውን ለመግታት በሚደረገው ርብርብ ላይ ብርቱ ጥርጣሬ ማሳየታቸው ተጨማሪ ተግዳሮት ኹኗል ። በአካባቢው ያሉ ግጭቶች መቀጠላቸውም የኢቦላ ተሐዋሲን ለመግታት እንቅፋት እየፈጠሩ መኾናቸው ተጠቅሷል ። እነዚህ ሁሉ ተግዳሮቶች የገጠሙት ይህ አዲስ አይነት የኤቦላ ተሐዋሲ በዋናነት እያጠቃ የሚገኘው ወጣቶችን መኾኑን ዶ/ር ዦን ካሴያ ተናግረዋል ።
«የምናወራው እጅግ ስለተጎዱ ዕድሜያቸው ከ15 እስከ 44 ዓመት ስለኾናቸው ወጣቶች ነው ። እነሱ እጅግ የተጎዱ መኾናቸውን ዕናውቃለን ። በእንቅስቃሴ እና በማዕድን ዘርፍ ላሉ የማኅበረሰብ ሚናዎች ተጋላጭ ናቸው ።»
የአፍሪቃ የበሽታ መቆጣጠሪያ እና መከላከያ ማእከላት ስለ አዲሱ ተሐዋሲ የግንዛቤ ለማስጨበጥ በጠራው ስብሰባ ላይ ዶ/ር ዦን ካሴያ የአካባቢው አገራት «አጋርነት በማሳየት ሚና እንዲኖራቸው» ግንዛቤ ማጨበጥም ወሳኝ መኾኑን ለመገናኛ አውታሮች ተናግረዋል ። የዩናይትድ ስቴትስ ዜጎች በኢቦላ ተሐዋሲ ቢያዙ ወደ ጀርመን አለያም ወደ ሌላ ለሕክምና ከመብረር ይልቅ ኬንያ ውስጥ ክትትል እንዲደረግላቸው 23 የለይቶ ማቆያ ማእከላት መዘጋጀታቸውንም ዶ/ሩ ይፋ አድርገዋል ።
የአፍሪቃ የበሽታ መቆጣጠሪያ እና መከላከያ ማእከላት ይፋ ባደረገው መረጃ፦ ለኢቦላ ቫይረስ ይበልጥ ተጋላጭ ሊኾኑ ይችላሉ ያላቸውን ኢትዮጵያን ጨምሮ 10 የአፍሪቃ አገራት ዘርዝሯል ። እንደ ኬንያ ሁሉ ሌሎች የአፍሪቃ አገራትም ዝግጅታቸውን እንዲያጠናክሩ ተነግሯቸዋል ። የኢቦላ ተሐዋሲን ለመግታት ርብርቡ ሊፋጠን ይገባልም ተብሏል ።
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ፀሐይ ጫኔ