ሰውሰራሽ አስተውሎት
ሐሙስ፣ የካቲት 7 2016ሰውሠራሽ አስተውሎት ወይም አርቲፊሻል ኢንተለጀንስን በመጠቀም በተንቀሳቃሽ ምስልና በፎቶ የተደገፉ ሐሰተኛ መረጃዎችን እየተበረካቱ መጥተዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩን ጨምሮ ሚኒስትሮች፣ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮችና ታዋቂ ግለሰቦች የዚህ ሃሰተኛ መረጃ ስርጭት ሰለባ እየሆኑ ነው።
ሰሞኑን የማሕበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ካጨናነቁት ሐሰተኛ መረጃዎች በጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድና ባለቤታቸው ላይ የተሰራ በሐሰት የተቀነባበረ ተንቀሳቃሽ ምስል ይገኝበታል። ከዚህ ውጭ የታዋቂ ጋዜጠኞችን ድምፅ ተጠቅሞ እገሌ የተባለ ባለሥልጣን ሞተ፣ እገሌ የተባለ አርቲስት በሚስጥር የተናገረው፤ በግንባር ላይ ያለ የታጣቂዎች አመራር የተጠለፈ የስልክ ንግግር ወዘተ እየተባለ በርካታ የድምጽ፣ የተንቀሳቃሽ ምስልና ፎቶ የተሳሳቱ መረጃዎች እየተሰረጩ ነው።
አቶ ሃብታሙ ታደሰ የተለያዮ መተግበሪያዎችን በማበልጸግ የሚታወቁና የዛይራይድ መስራች ናቸው።በሰው ሠራሽ አስተውሎት ስለሚቀናበሩ ሐሰተኛ መረጃዎች እንዲህ አጫወቱን
``በአሁኑ ሰዓት ከአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ጋር ተያይዞ ብዙ ሶፍትዌሮች መጥተዋል። በመሆኑም የእንትና ድምጽ ተቀድቶ ወጣ እየተባሉ የሚሰራጩ ሐሰተኛ መጃዎች አሉ። ቴክኖሎጂው ይህን ለመስራት ነገሮችን አቅልሎታል።``
አቶ ሃብታሙ በሰው ሠራሽ አስተውሎት ተቀናብረው የሚሰራጩ ሐሰተኛ መረጃዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየበረከቱ መምጣታቸውንም አክለዋል።
ለረዥም ዓመታት በኢንፎርሜሽን ኮሚዩኒኬሽን ፕሮግራሞችን በመስራት የሚታወቀውና በአሁኑ ሰአት የመገናኛ ብዙሃን አማካሪ የሆነው ጋዜጠኛ ሃበንዮም ሲሳይ በሰው ሠራሽ አስተውሎት ተሰርተው የሚሰራጩ ሐሰተኛ መረጃዎች ሕብረተሰቡን እያደናገሩት እንደሆነ ማስተዋሉን ነግሮናል።
`` በአርቲፊሻል ኢንተለጀንስ ተጠቅመው ስሜቱንም ጭምር ለማንጸባረቅ በሚያስችል መልኩ የሐሰት መረጃዎች ተቀናብረው እየተሰራጩ ይገናሉ።``
የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ተጠቃሚዎች የሚያሰራጩአቸውን መረጃዎች ለሌላ ሰው ከማጋራታቸው በፊትእውነተኛነታቸውን ማረጋገጥ እንደሚገባ ጋዜጠኛ ሃበንዮም አሳስቧል።
ሰው ሠራሽ አስተውሎትን በመጠቀም ተቀናብረው የሚሰራጩ መረጃዎች የሚያስከትሉት አሉታዊ ተጽዕኖ እጅግ የከፋ መሆኑን የጠቀሱት ባለሙያዎቹ የማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ተጠቃሚዎች በወጉ ያልተጣሩ መረጃዎችን ከማጋራት እንዲቆጠቡም መክረዋል።
ዮሐንስ ገብረእግዚአብሔር
ሽዋዬ ለገሰ