1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ህወሓትን እና ክስ ተቋርጦ የተፈቱ ፖለቲከኞችን አስጠነቀቁ

እሑድ፣ ጥር 1 2014

ጠቅላይ ምኒስትር ዐቢይ አሕመድ "በግራ በቀኝ ሊነካካን ይሞክራል" ላሉት ህወሓት "አትንኩን፣ እረፉ" የሚል ማስጠንቀቂያ ሰጥተዋል። ተቃውሞ የገጠመው ክስ በማቋረጥ ፖለቲከኞችን የመፍታት ውሳኔ "እየመረረን የዋጥንው እውነት ነው" ሲሉ ገልጸውታል። "የኢትዮጵያን ዘርፈ-ብዙ ጠላቶች የሚቀንስ" መሆኑን ጠቅሰው የተቃወሙ እንዲቀበሉ ጠይቀዋል።

https://p.dw.com/p/45K2H
Äthiopien | Premierminister Abiy Ahmed Ali
ምስል Minasse Wondimu Hailu/AA/picture alliance

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ላለፈው አንድ አመት ከመንግሥታቸው ለተዋጋው ህወሓት እና ክሳቸው ተቋርጦ ለተፈቱ ፖለቲከኞች ማስጠንቀቂያ ሰጡ። በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ ለወታደሮች እና የጦሩ ከፍተኛ አመራሮች ሽልማት ሲሰጥ ባደረጉት ንግግር መንግሥታቸው የህወሓት አመራሮችን ከእስር በመፍታቱ ለቀረበበት ተቃውሞ ምላሽ ሰጥተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ዛሬ ጥር 1 ቀን 2014 ዓ.ም. ባስመረቀው ዋና መሥሪያ ቤት በተካሔደው ሥነ-ሥርዓት ላይ ባደረጉት ንግግር ባለፉት አመታት ህዝባዊ ወያነ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) ሰራቸው ያሏቸውን ስድስት ስህተቶች ዘርዝረው አቅርበዋል። ህወሓት "ለሁለት ተከፍሎ ከፊሉ ብልጽግና [ፓርቲ] ጋር መቆየት ቢችል ኖሮ በርካታ ዜጎቹን መታደግ ይችል ነበር" ሲሉ ተደምጠዋል።

ህወሓት ከኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት በሚቃረን መንገድ "የምርጫ ኮሚቴ በመሰየም ምርጫ ለማድረግ የዳዳበት ሁኔታ እጅግ ዋጋ አስከፍሎታል" ያሉት ዐቢይ በሰሜን ዕዝ ላይ የተፈጸመውን ጥቃትም ጠቅሰዋል። የኢትዮጵያ ጦር ከትግራይ ክልል ሲወጣ "ወጡልኝ ብሎ ከሚከተል ደጋግሞ ቢያስብ ኖሮ የብዙ ወጣቶች ሕይወት ከመቀጠፍ ያድን ነበር" በማለት ተናግረዋል።

"አሁንም ህወሓት በግራ በቀኝ ሊነካካን ይሞክራል" ያሉት ዐቢይ "ለሰባተኛ ስህተት የሚጓዘው ህወሓት በፍጹም ድል የማግኘት እንኳ ቢሆን በወጣት የትግራይ ልጆች ላይ በሕይወት የመቀጠፍ፣ የመቁሰል አደጋ የሚያስከትል ስለሆነ ሰባተኛው ስህተቱ መስመር ስቶ ሳይሄድ መማር የሚችልበት ዕድል መፍጠር የራሱ ቢሆንም እንኳ እንደ ባላንጣ አትንኩን፣ እረፉ ለማለት እወዳለሁ" ሲሉ ተደምጠዋል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ "የነካካችሁን እንደሆነ በተለመደው መንገድ የከፋ ቅጣት ይደርስባችኋል" ሲሉ አስጠንቅቀዋል።

Äthiopien Tigray | Hauptstadt Mekele | TPLF-Zentrale
ምስል EDUARDO SOTERAS/AFP/Getty Images

ዐቢይ ረዘም ባለ ንግግራቸው የኢትዮጵያ መንግሥት በእስር ላይ የነበሩ ፖለቲከኞችን ክስ በማቋረጥ ለመፍታት የደረሰበት ውሳኔ ለገጠመው ተቃውሞ ምላሽ ሰጥተዋል።

ከትናንት በስቲያ መንግሥት የኦሮሞ ፌድራሊስት ኮንግረስ፣ የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ አመራሮችን እና በሰሜን ኢትዮጵያ ውጊያ ከተቀሰቀሰ በኋላ በምርኮ ተይዘው የታሰሩ አንጋፋ የህወሓት አመራሮችን ክስ በማቋረጥ እንዲፈቱ ወስኗል።

"ትናንት ክስ አቋርጠን ከእስር ቤት እንዲፈቱ ያደረግናቸው ግለሰቦች ሁሉም በሚባል ደረጃ የመንግሥት ሥልጣን ይዘው በዚህ ሁኔታ ውስጥ የተሳተፉ፣ በቀጥታ የሚወስኑ የሚያዙ አይደሉም" ያሉት ዐቢይ በውሳኔው ላይ የተሰነዘረው ተቃውሞ ከሁለት ጎራ እንደተቀሰቀሰ ጠቅሰው "ቅን" ላሉት ምላሽ ሰጥተዋል።

የታሰሩ ፖለቲከኞችን ክስ አቋርጦ የመፍታት ውሳኔ የተቃወሙ ወገኖች "እኛም መጀመሪያ ስንሰማው ያስደነገጠን መሆኑን" እንዲገነዘቡላቸው ጠይቀዋል። ውሳኔው "ለኢትዮጵያ የሚበጅ፣ ለኢትዮጵያ ዘላቂ ጥቅም የሚያግዝ፤ የኢትዮጵያን ዘርፈ-ብዙ ጠላቶች የሚቀንስ በአውደ ውጊያ ያገኘንውን ድል በሰላሙም መንገድ እንድንደግም የሚያደርግ የአባቶቻችን ልጆች መሆናችንን የሚያረጋግጥ" ሲሉ ገልጸውታል።  "እየመረረን የዋጥንው እውነት ነው" ያሉትን ውሳኔ የተቃወሙ ወገኖች "እናንተም ለሀገራችሁ ዘላቂ ድል ስትሉ፤ ለሀገራችሁ ክብር እና አሸናፊነት ስትሉ ደጋግማችሁ በማሰብ ይኸንን ውሳኔ እንድትቀበሉ በትህትና እጠይቃችኋለሁ" የሚል መልዕት አስተላልፈውላቸዋል።

የሰሜን ኢትዮጵያ ጦርነት በጥቅምት 2013 ዓ.ም. ከተጀመረ በኋላ ከታሰሩ የህወሓት አመራሮች መካከል አቶ ስብሐት ነጋ፣ ወይዘሮ ቅዱሳን ነጋ፣ አቶ አባይ ወልዱ፣ አቶ አባዲ ዘሙ፣ ወይዘሮ ሙሉ ገብረ እግዚዓብሔር እና አቶ ኪሮስ ሐጎስ ተቃውሞ በገጠመው የኢትዮጵያ መንግሥት ውሳኔ ይፈታሉ።

ከህወሓት አመራሮች በተጨማሪ የኦሮሞ ፌድራሊስት ኮንግረስ አመራሮች የሆኑት አቶ ጃዋር መሐመድ እና አቶ በቀለ ገርባ፤ የባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ አመራሮች አቶ እስክንድር ነጋ እና አቶ ስንታየሁ ቸኮልን ጨምሮ በርከት ያሉ ፖለቲከኞች ተፈተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ክስ የተቋረጠላቸው እና ከእስር የተፈቱ ፖለቲከኞች "እናንተን ሳይሆን ከእናንተ ጀርባ ያለውን ሕዝብ አክብረን የወሰንን መሆናችንን አውቃችሁ ይኸን ዕድል ሳታበላሹ እንድትጠቀሙበት" ብለዋል። "ክስ ማቋረጥ ምህረት አይደለም" ያሉት ዐቢይ መንግሥታቸው የክስ መዝገብ መልሶ ሊመዝ እንደሚችል ጥቆማ ሰጥተዋል።

እሸቴ በቀለ

ታምራት ዲንሳ