ጀርመናዊትዋ የመከላከያ ሚኒስትር ለአውሮጳ ኮሚሽን ፕሬዚደንትነት ታጩ
ረቡዕ፣ ሰኔ 26 2011ማስታወቂያ
የአውሮጳ ኅብረት ሃገራት ርእሳነ-ብሔራት እና ፕሬዚደንቶች ዛሬ ብራስልስ ውስጥ በጠሩት ልዩ ስብሰባ የጀርመን የመከላከያ ሚኒስትር ዑርዙላ ፎንደር ላይንን ለአውሮጳ ኮሚሽን ፕሬዚደንትነት በእጩነት መቅረባቸዉ ተሰማ። ብራስልስ በሚገኘዉ የኅብረቱ ጽ/ቤት ዛሬ የተጠራዉ ስብሰባ የጀመረዉ ከአምስት ሰዓታት መራዘም በኋላ መሆኑን ታዉቋል። ስብሰባው የተጠራው የኅብረቱ ኮሚሽን ፕሬዝዳንት ዦን ክላውድ ዩንከርን የሚተካ ባለሥልጣን ለመምረጥ ነው። የአውሮጳ ምክር ቤት ፕሬዚደንት ዶናልድ ቱስክ እና በቅርቡ ስልጣናቸዉን ለተተኪ የሚያስረክቡት የኅብረቱ ኮሚሽን ፕሬዝዳንት ዦን ክላውድ ዩንከር የአውሮጳ መሪዎች የጀርመን መከላከያ ሚንስትር ዑርዙላ ፎንደር ላይንን የኮሚሽኑ ፕሬዚደንት እንዲሆኑ ድጋፋቸውን እንዲሰጡ እንደሚጠይቁ ስብሰባዉ ከመጀመሩ ቀደም ሲል ተሰምቶ ነበር። ርእሳነ-ብሔራት እና ፕሬዚደንቶች የጀርመን የመከላከያ ሚኒስትር ዑርዙላ ፎንደር ላይንን በእጩነት ይምረጡ እንጂ ምርጫዉን የአዉሮጳ ፓርላማ እንዲያፀድቀዉ ይጠበቃል። የምክር ቤቱ ዉሳኔ ከሁለት ሳምንት በኋላ ይፋ ይሆናል ተብሎ ይጠበቃል። የአዉሮጳ ምክር ቤት በእጩነት የቀረቡትን ዉድቅ ቢያደርግ የአውሮጳ ኅብረት ሃገራት ርእሳነ-ብሔራት እና ፕሬዚደንቶች ዳግም ሌላ እጩ መሰየም ይኖርባቸዋል።
አዜብ ታደሰ
ኂሩት መለሰ