ከሳምንታት የአገልግሎት መስተጓጎል በኃላ ዳዳብ ወደ ስራ ተመልሷል
ማክሰኞ፣ ታኅሣሥ 10 2010ላለፉት ሶስት ሳምንታት ያክል አገልግሎት መስጠት ዐቆሞ የነበረው የዓለም ትልቁ የስደተኞች መጠለያ ጣቢያ ዳዳብ ዳግም ስራውን ጀምሯል፡፡
ጣቢያው ስራውን እንዲያቆም ምክንያት የሆነውን ተቃውሞ ያስነሱ የዙሪያው ማህበረሰብ አባላት እና የተባበሩት መንግስታት ከፍተኛ ኮሚሽን ለስደተኞች በምህጸረ ቃሉ UNHCR የወከሉ ባለስልጣናት ያደረጉትን ውይይት እና ድርድር ተከትሎ ነው አገልግሎቱን ለመቀጠል የቻለው፡፡
በውይይቱ ወቅት የዳዳብ ዙሪያ ማህበረሰብ ከወከሉት አንዱ ሞሀመድ ዳዬ (የፓርላማ አባልም ናቸው) በአካባቢው ነዋሪዎች ዘንድ አሳሳቢ የሆኑ ከስደተኛ መጠለያው ጋር የተገናኙ ጉዳዮችን አንስተዋል፡፡ በጣቢያው ውስጥ ይሰሩ የነበሩ የአካባቢው ሰዎችን ከስራ መቀነስ እና ስደተኞች ለሃይል ምንጭነት የተፈጥሮ ሀብቶችን ማራቆታቸውን በተመለከተ የቀደሙ አሰራሮችን ተችተዋል፡፡
‹‹የሰራተኞች ቅነሳ ስደተኞችንን ያስጠለለውን ማህበረሰብ በአሉታዊ መልኩ ተጽዕኖ ፈጥሮበታል ብለን እናምናለን፡፡በተሸለ ሁኔታ መከወን ይችል ነበር የሚል ዕምነም አለን፡፡
በአከባቢ ጥበቃና ሃይል ላይ በሚንቀሳቀሱ ግብረሰናይ ድርጅቶች ፤ በማህበረሰብ ነክ ፕሮጀክቶች የሚነሱ ጉዳዮችም አሉ ፡፡ቀደም ብሎ የተወሰደው ርምጃ የባለሙያ ምክክር ነበረበት ብለንም አናምንም፡፡›› ብለዋል፡፡
አራት ሠኣታትን በፈጀው የሁለቱ አካላት ቆይታ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከፍተኛ ልዑካን አባላት በበኩላቸው የመሰል ንግግርና ድርድሮችን መፈጠር በበጎ ካዩት በኃላ ከማህበረሰቡ አባላት ለወደፊቱ ቢታሰብባቸው ያሉ ነጥቦችን አንስተዋል፡፡
‹‹መነጋገራችን መቀጠል አለበት፡፡ቀደም ብሎ እንደነበረው አገልግሎቶች ሳይቆረጡ ሰዎች የሚናገሩበት እና የሚደራደሩበት አሰራር ያስፈልገናል፡፡አሁን እያየነው ያለው አዲስ ልማድ ፤አገልግሎቶችን ማገድ እና መዝጋት ስልጡንነት የጎደለውና በመቶ እና ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ህይወት ላይ ጫና እየፈጠረ ነው፡፡›› ብለዋል፡፡
የማህበረሰቡ እና የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከፍተኛ ኮሚሽን ለስደተኞች ተወካዮች በመሰረታዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት ላይ በመድረሳቸው መደበኛ እና ከዓመታት በፊት ተቋርጠው የነበሩ አገልግሎቶች እንደ አዲስ መሰጠት ጀምረዋል፡፡ከዚህ ቀደም ባሰማነው ዘገባ ላይ ስለ ዳዳብ ወቅታዊ ሁኔታ ያጋሩንን አቶ አለማየሁ ሆርዶፋን በድጋሚ አግኝቻቸዋለሁ ፤በአሁኑ ወቅት ስላለው የመጠለያ ጣቢያው ውስጥ እንቅስቃሴ ነግረውኛል፡፡
ሀብታሙ ስዩም
ሸዋዬ ለገሠ