ደቡብ ምዕራብ ሕዝቦች ክልል የተከሰተው የተምች ወረርሽኝ
ዓርብ፣ ግንቦት 19 2014በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል የተምች ወረርሽኝ መከሰቱን የክልሉ አርሶ አደሮች ገለጹ። አርሶ አደሮቹ እንዳሉት በአካባቢያቸው ከባለፈው ሳምንት አጋማሽ ጀምሮ የተከሰተው የተምች ወረርሽኝ በበቆሎና በሩዝ ማሳዎቻቸው ላይ ጉዳት እያደረሰ ይገኛል። የተምች ወረርሽኙ በክልሉ 12 ወረዳዎች ውስጥ በ1 ሺህ 219 ሄክታር መሬት ላይ መከሰቱን ለዶቼ ቬለ (DW) የገለጹት የክልሉ ግብርና ጽ/ቤት ምክትል ኃላፊ አቶ አሸናፊ ክንፉ በአሁኑ ወቅትም ወረርሽኙን በባህላዊና በዘመናዊ የመከላከያ ዘዴዎች ለመቆጣጠር ጥረት እየተደረገ ይገኛል ብለዋል።
በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች የሚገኙ አርሶ አደሮች እንዳሉት የተምች ወረርሽኙ በአካባቢያቸው መታየት የጀመረው ከባለፈው ሳምንት አጋማሽ ጀምሮ ነው። በተለይም በክልሉ በሰብል አምራችነቱ በሚታወቀው የቤንች ሸኮ ዞን ጉራፈርዳ ወረዳ ወረርሽኙ በስፋት መታየቱን ነዋሪዎቹ ተናግረዋል።
በዞኑ ጉራፈርዳ ወረዳ የኩጃ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑት አርሶአደር ጎቻው አይተንፍሱ እና ገበየሁ አማረ የተምች ወረርሽኙ የተከሰተው ሰሞኑን በአካባቢያቸው በካፊያ መልክ የጣለውን ዝናብ ተከትሎ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ወረርሽኙ አሁንባለው ሁኔታ በደረሱ የቦቆሎና የሩዝ ሰብሎች ላይ ጉዳት እያደረሰ እንደሚገኝ የጠቀሱት አርሶአደሮቹ በዚህም የምርት መቀነስ ሊያጋጥም ይችላል የሚል ሥጋት እንዳደረባቸው ተናግረዋል።
በደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ክልል ያጋጠመው የተምች ወረርሽኝ በቅድሚያ በክልሉ ከፋ ዞን ከተከሰተ በኋላ በቀናት ልዩነት በሌሎች አካባቢዎችም መታየቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታውቋል። የግብርና ጽ/ቤቱ ምክትል ኃላፊ አቶ አሸናፊ ክንፉ በአሁኑወቅት ወረርሽኙ በክልሉ 4 ዞኖች ውስጥ በሚገኙ 12 ወረዳዎች ውስጥ በ 1 ሺህ 219 ሄክታር መሬት ላይ መታየቱን ነው ለዶቼ ቬለ የገለጹት። በአሁኑ ወቅት በክልሉ የተከሰተውን የተምች ወረርሽኝ በባህላዊና በዘመናዊ የመከላከያ ዘዴዎች ለመቆጣጠር ጥረት በመደረግ ላይ እንደሚገኝም ምክትል ኃላፊ ተናግረዋል።
ሸዋንግዛው ወጋየሁ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ሸዋዬ ለገሰ