የፖለቲካ ፓርቲዎች የእስር ዘመቻውን አወገዙ
ማክሰኞ፣ ግንቦት 16 2014ማስታወቂያ
መንግሥት ከሰሞኑ በግለሰቦች ላይ የጀመረው እሥር እና የኃይል አፈና አገርን ወደ ከፋ ውስብስብ ቀውስ የሚያስገባ ነው ሲሉ ሁለት ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ርምጃውን ነቀፉ። ኅብር ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ በወታደራዊ ኃይል ሕግን ማስከበር፣ የሕዝብ ሥልጣንን መቆጣጠርም ሆነ ሠላምና መረጋጋትን ማስፈን አይቻልም ሲል በተለያየ ሞያ ውስጥ ያሉ ሰዎች ላይ የተወሰደውን የእሥር ርምጃ ኮንኖታል። ፓርቲው ባለፉት አራት ዓመታት ኢትዮጵያ ከመቸውም ጊዜ በባሰ መልኩ ችግር ውስጥ መግባቷን ተናግሮ መንግሥት ከያዘው የጥፋት ያለው መንገድ እንዲወጣም ጠይቋል። ባልደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ በበኩሉ በአሁኑ ወቅት ከ12 የማያንሱ አባላቶቹ እንዲሁም በተለያየ የሞያ ዘርፎች ውስጥ ያሉ ግለሰቦች በእሥር ላይ መሆናቸውን ተናግራል። ፓርቲው ታሳሪዎቹ በአስቸኳይ እንዲለቀቁም ጠይቃል። ፓርቲው የመንግስት ርምጃ ሕዝብን ወደ ሕዝባዊ አመጽ እንዲሸጋገር የሚገፋ በመሆኑ ሊታረም ይገባል ብሏል። መንግሥት በበኩሉ በሕገ ወጥ ተግባራት ላይ በመሳተፍ ኹከትና ብጥብጥ እንዲፈጠር ሆን ብለው በሚሰሩ ባላቸው አካላት ላይ የሚወስደውን ርምጃ እንደሚቀጥልበት ከሰሞኑ ተናግራል።
ሰለሞን ሙጬ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ሸዋዬ ለገሰ