1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የድምጻዊ ሃጫሉ ግድያና የኦፌኮ እስርን በመቃወም የተቃዉሞ ሰልፍ በፍራንክፈርት

ዓርብ፣ ሰኔ 26 2012

የኦሮሞ ብሄር ተወላጆች የታዋቂውን ድምፃዊና የነጻነት ታጋይ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያና የ/ኦፌኮ/ አመራሮችን እስር በመቃወም ዛሬ በፍራንክፈርት ከተማ ሰላማዊ ሰልፍ አካሂደዋል:: በፍራንክፈርት የኢትዮጵያ ቆንጽላ ጄኔራል ጽ/ቤትና በተለያዩ የከተማዋ አደባባዮች ተቃውሞዋቸውን አሰምተዋል::

https://p.dw.com/p/3el8k
Deutschland Protest gegen Mord an Hachalu Hundessa in Frakfurt
ምስል DW/E. Fekade

 

ዛሬ ከቀትር በኋላ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ኢትዮጵያውያን የኦሮሞ ብሄር ተወላጆች የታዋቂውን ድምፃዊና የነጻነት ታጋይ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያና የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ /ኦፌኮ/ አመራሮችን እስር በመቃወም የተለያዩ መፈክሮችን እና መልክቶችን በማሰማት በፍራንክፈርት የኢትዮጵያ ቆንጽላ ጄኔራል ጽ/ቤትና በከተማዋ አደባባዮች ቁጣቸውን ለመግለፅና ድምፃቸውን ለዓለማቀፉ ማህበረሰብ ለማሰማት ለተወሰኑ ደቂቃዎች መንገድ በመዝጋት ጭምር የታገዘ ሰላማዊ ሰልፍ አካሂደዋል:: በከፍተኛ ቁጣ የተሞሉት ሰለፈኞቹ "ከዕውቁ ድምፃዊ ሃጫሉ ሁንዴሳ ግድያ ጀርባ የገዢው መንግስት እጅ አለበት" ሲሉ ወቅሰዋል:: ከ 5ሺ በላይ ቄሮዎች ሕይወታቸውን ገብረው ጨቋኙን ስርዓት የለወጡት ሕብረ ብሄራዊ ሥርዓቱን በመናድ አሃዳዊ መንግስትን የሚገነባ ፈላጭ ቆራጭ አምባገነን አስተዳደርን ለመተካት አይደለም ያሉት ሰልፈኞቹ ፤ በፖለቲካ ሴራ የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ /ኦፌኮ/ አመራር የሆኑት አቶ በቀለ ገርባ እንዲሁም የፓርቲው አባልና አክቲቪስት አቶ ጃዋር መሃመድን ጨምሮ ሌሎችም ግለሰቦች መንግሥት ባቀነባበረው የፖለቲካ ሴራ ለእስር መዳረጋቸውንም አጥብቀው ተቃውመዋል:: የሰልፉ አስተባባሪ አቶ አብዶቃዲ አባጀበል መንግስት በርካታ ንፁሃን ኦሮሞዎችን እየገደለና እያሰረ የሚገኝበት ሰቆቃ እንዲያበቃ ፤ የፖለቲካ እስረኞች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ በአስቸኳይ እንዲፈቱና ገዢው መንግስት ከተቃዋሚ ኃይሎች ጋር አስቸኳይ ውይይት በማካሄድ በሰላማዊ መንገድ ስልጣኑን እንዲለቅ ለመጠየቅ ሰልፉ መጠራቱን ለዶይቼ ቨለ "DW" ገልፀዋል:: ሌላዋ ሰልፈኛ ቀነኒት አብዲም በኦሮሞዎች ላይ የሚፈፀመው ግድያና እስራት በአስቸኳይ ይቁም ከተቃዋሚ ኃይሎች ጋር መንግሥት ሰላማዊ ውይይትና ድርድር ይጀምር ብለዋል::
እኛ ኢትዮጵያን የመገንባት እንጂ የማፍረስ ዓላማ የለንም ያሉት ሰልፈኞቹ ፤ ጥያቄያቸው ምላሽ እስኪያገኝ በአገር ውስጥም ሆነ በዲያስፖራ ጠንካራ የተቃውሞ እንቅስቃሴዎችን እንደሚያካሂዱ አስታውቀዋል:: ቄሮ የታገለው ኢትዮጵያን ከመፍረስ ለማዳን ነው ያሉት በሰልፉ ላይ ያነጋገርናቸው አስተያየት ሰጪዎች ያም ቢሆን ጥያቄያችን የማይመለስ ከሆነ የማይቀረውን አማራጭ ለመግፋት እንገደዳለን ሲሉም ተናግረዋል::መላው የኢትዮጵያ ብሔረሰቦችም ሰላማዊ ትግላቸውን እንዲደግፉ ጥሪ አስተላልፈዋል:: በድርጊቱ የተቆጡ አንዳንድ ሰልፈኞች በስፍራው በስራ ላይ በነበርንበት ወቅት "የመንግስት ወኪል ነው" በማለት ለመተናኮል ቢሞክሩም ፤በርካታ የጀርመን የፖሊስ ኃይል በቦታው በመኖሩ ከጥቃት ለመትረፍ ችለናል :: የሰልፉ አስተባባሪ አቶ አብዶቃዲ አባጀበል ካለመግባባት ለተፈጠረው ስህተት ይቅርታ ጠይቀዋል::


እንዳልካቸው ፈቃደ

እሸቴ በቀለ