የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ሕዝበ-ውሳኔ አስራ አንደኛው ክልል እንዲቋቋም ወሰነ
ቅዳሜ፣ መስከረም 29 2014ማስታወቂያ
በደቡብ ክልል አምስት ዞኖች እና አንድ ልዩ ወረዳ የተካሔደው ሕዝበ-ውሳኔ አስራ አንደኛው የኢትዮጵያ ክልል እንዲቋቋም ወሰነ። የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የሕዝበ-ውሳኔን ውጤት ዛሬ ቅዳሜ መስከረም 29 ቀን 2014 ዓ.ም. ይፋ አድርጓል። ውጤቱ ለኢትዮጵያ የፌዴሬሽን ምክር ቤት ይቀርባል።
በምዕራብ ኦሞ፣ ቤንች ሸኮ፣ ካፋ፣ ዳውሮ እና ሸካ ዞኖች እንዲሁም የኮንታ ልዩ ወረዳ ሕዝበ-ውሳኔ የተካሔደው ባለፈው መስከረም 20 ቀን 2014 ዓ.ም. ነበር።
አምስቱ ዞኖች እና አንዱ ልዩ ወረዳ "ከደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል ወጥተው የጋራ አንድ ክልል መመሥረታቸውን እደግፋለሁ" የሚለው አማራጭ 1 ሚሊዮን 221 ሺሕ 92 ድምጾች ማግኘቱን የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ምክትል ሰብሳቢ አቶ ውብሸት አየለ ይፋ አድርገዋል።
"የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልል አካል ሆነው መቀጠላቸውን እደግፋለሁ" የሚለው ምርጫ በአንጻሩ 24 ሺሕ 24 ድምጽ ማግኘቱን አቶ ውብሸት ገልጸዋል።
በውጤቱ መሠረት አምስቱ ዞኖች እና አንዱ ልዩ ወረዳ ከደቡብ ክልል ወጥተው የጋራ አንድ ክልል ይመሰርታሉ። ይኸ ለኢትዮጵያ ፌድራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ አስራ አንደኛው ክልል ይሆናል።
ሰለሞን ሙጬ
እሸቴ በቀለ