1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ አማራዎች መመለስ

ሐሙስ፣ ግንቦት 19 2013

ከዓመታት በፊት በማንነታቸው አካባቢያቸውን ለቅቀው የነበሩ የወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ የአማራ ተወላጆች ወደቀያቸው መመለስ መጀመራቸውን የዞኑ አስተዳደር ዐስታወቀ። ባለፉት ዓመታት ከ50 ሺህ በላይ አማራዎች ከቀያቸው መፈናቀላቸውን አስተዳደሩ አመልክቷል።   

https://p.dw.com/p/3u3pN
Äthiopien | Ashete Demilew
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

«ከ50 ሺህ በላይ አማራዎች ከቀያቸው ተፈናቅለዋል»

ከዓመታት በፊት በማንነታቸው አካባቢያቸውን ለቅቀው የነበሩ የወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ የአማራ ተወላጆች ወደቀያቸው መመለስ መጀመራቸውን የዞኑ አስተዳደር ዐስታወቀ። ባለፉት ዓመታት ከ50 ሺህ በላይ አማራዎች ከቀያቸው መፈናቀላቸውን አስተዳደሩ አመልክቷል።   

አካባቢው ቀድሞው ጎንደር ክፍለ ሀገር ተብሎ ይጠራ በነበረበት ወቅት የአማራ ተወላጆች ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር ይኖሩበት እንደነበርና የኢህአዴግ መንግስት ስልጣን ከያዘ በኋላ አካባቢው ያለ ነዋሪዎቹ ፈቃድ በትግራይ ክልል እንዲካለል ሆኖ መቆየቱንና  “ለምን” ብለው የጠየቁ አካላት መገደላቸውን፣ መሰደዳቸውንና መፈናቀላቸውን የወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ ዋና አስተዳዳሪ አቶ አሸተ ደምለው ተናግረዋል፡፡

እንደ አቶ አሸተ ባለፉት 30 ዓመታት ህወሓት አካባበውን ባስተዳደረበት ወቅት የአማራ ባህል፣ እሴትና ማንነት እንዲጠፋ መደረጉንና 500 ሺህ የሚገመት የወልቃት ጠገዴ የአማራ ተወላጅ መፈናቀሉንና በተለያዩ ክልሎችና አገሮች መሰደዱን ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል፡፡ 30ሺህ በጎረቤት ሱዳን ኖራሉ ብለዋል፡፡

የአካባው ነዋሪዎች ማንነት ተከብሮና ታውቆ አካባቢውም ወደ አማራ ክልል እንዲደራጅ ረጅም ትግል መደረጉንና መስዋዕት መከፈሉን የተናገሩት አቶ አሸተ እውነትን የያዘ አሸናፊነቱ የተረጋገጠ በመሆኑ በህዝብ ልጆች መስዋዕትነት አሁን አካባበው በራሱ ልጆች እየተዳደረ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

ከቀያቸው ተፈናቅለው ለዓመታት በስደት የኖሩ የአካባቢው ተወላጆችም ወደ ትውልድ ቦታቸው መመለስ መጀመራቸውን ዋና አስተዳዳሪው ተናግረዋል፡፡

የዞኑ አስተዳደር ቀደም ሲል በነበረው አስተዳደር ይደርሳባቸው የነበረውን ግፍና በደል ሸሽተው የነበሩ ወገኖችን መልሶ ለማቋቋም የአካባበውን ሰላም አስተማማኝ ለማድረግ እየሰራ መሆኑን ጠቁመው አስፈላጊ የሆኑ መሰረታዊ ፍላጎቶች እንዲሟሉላቸውም  እንደሚደረግ ገልፀዋል፡፡

እስካሁን ከሱዳን ብቻ አንድ ሺህ አንድ መቶ አስራ አንድ  (289  አባወራ እና 822 ቤተሰብ) የሚሆኑ የአካባቢው ነዋሪዎች መመለሳቸውን የተናገሩት አቶ አሸተ የሰላምና መረጋጋቱ ሁኔታ እየተሸሻለ ሲመጣ ሁሉም ወደ ቀያቸው መለሳሉ የሚል እምነት እንዳላቸው  አመልክተዋል፡፡

ህብረተሰቡ የአካባቢው ነዋሪ ማንነት እንዲመለስለት እንዳደረገው ትግል፣ አሁንም ተፈናቅለው ለዓመታት በሌላ አካባቢ ሲንገላቱ የነበሩ ወገኖችን መልሶ ለማቋቋም በሚደረገው ትረት የራሱን ድርሻ እንዲወጣ አደራ ብለዋል፡፡

የፌደራሉ መንግሰት ቀደም ሲል በህጋዊ መንገድ የተጀመረውን የፍትህና የማንነት ጥያቄ በአፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጥበትም ጠይቀዋል፣ ዋና አስተዳዳሪው አያይዘውም መንግስት በቀጣዩ በጀት ዓመት ለዞኑ የስራ ማስኪያጃና የካፒታል በጀት ማስፈፀሚ በጀት እንዲመድብለት ጠይቀዋል፡፡

የወልቃይት ጠገዴ ሰቲት ሁመራ  ዞን ሰሞኑን አካባቢው ማንነቱን እንዲመልስ ላደረጉ ባለድርሻ አካላት እውቅና ሰጥቷል፣ ምስጋናም አቅርቧል፡፡

ዓለምነው መኮንን

ማንተጋፍቶት ስለሺ

ሸዋዬ ለገሰ