የኢትዮጵያዉያን የድረሱልን ጥሪ በደቡብ አፍሪቃ
ሐሙስ፣ ነሐሴ 2 2011በደቡብ አፍሪቃ ጆሃንስበርግ ከተማ ፖሊስ ሕገ-ወጥ ያላቸዉን ወደ 600 አፍሪቃዉያንን በቁጥጥር ስር ማዋሉ ተገለፀ። ከታሰሩት መካከል ከ 250 በላይ የሚሆኑቱ ኢትዮጵያዉያን ናቸዉ ያሉን በደቡብ አፍሪቃ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪ እና ጋዜጠኛ መላኩ አየለ እንደሚሉት ፖሊስ ያሰራቸዉ ኢትዮጵያዉያን የመኖርያ ፈቃድ ያላቸዉ ናቸዉ፤ ልጆቻቸዉ ትምህርት ቤት የነበሩ እናት እና አባት ሳይቀሩ መታሰራቸዉን ተናግረዋል። በደቡብ አፍሪቃ የሚገኙ ኢትዮጵያዉያን ተግተዉ ሰራተኞች በመሆናቸዉ ኢትዮጵያዉያን ላይ ያነጣጠረ ጥቃት ነዉ ሲሉ ኢትዮጵያዉያን የድረሱልን ጥሪ እያሰሙ መሆናቸዉን ተናግረዋል። በሃገሪቱ ደንብ መሰረት በቁጥጥር ስር የዋለ ግለሰብ በ 24 ሰዓት ዉስጥ ፍርድ ቤት እንዲቀርብ ቢደነግግም በአንድ ላይ ታጉረዉ ታስረዉ የሚገኙት ኢትዮጵያዉያን አሁንም የፍትህ አካል እንዳላገኛቸዉም ታዉቋል። በደቡብ አፍሪቃ የመገናኛ ብዙኃን ዘገባ መሰረት ከታሰሩት 600 ሕገወጥ ግለሰቦች መካከል ኢትዮጵያዉያን ሶማልያዉያን ዚምባቡያዉያን እና ከማላዊ የመጤ ዜጎች ይገኙበታል። ጆሃንስበርግ የሃበሾች ንግድ እንቅስቃሴ በስፋት የሚከናወንባቸው ጂፒ፣ ዴልቨርስ፣ትሮይ፣ቫንቬለህ እና ስሞል ስትሬት የተባሉት ጎዳናዎች ዛሬ ሙሉ በሙሉ ተዘግተዉ መዋላቸዉን በደቡብ አፍሪቃ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪና ጋዜጠኛ መላኩ አየለ ለዶቼ ቬሌ ተናግረዋል። ሙሉ ቃለ ምልልሱ እንደሚከተለዉ ይቀርባል።
አዜብ ታደሰ
ኂሩት መለሰ