የኢትዮጵያዉያን የኪነ-ጥበብ መድረክ ጥሪ
ሐሙስ፣ ሰኔ 11 2012«የፊልም ስራተኞች ለምሳሉ አብዛኛዉን ጊዜ በየሰዉ ቤት በየተለያዩ መስራቤቶች እንዲሁም በየመንገድ ላይ ነዉ ፊልማቸዉን የሚቀርፁት አሁን ግን በኮሮና እና በታወጀዉ አስቸኳይ ጊዜ ምክንያት መሰብሰብ አይቻልም ፤ ፊልም መስራት አልተቻለም ። ሁሉም ሰራተኞች ማለት ይቻላል፤ የመንግሥት ተቀጣሪ አይደሉም፤ በጣም ችግር ላይ ነን፤ መንግሥትና ሕዝብ ሊደርስልን ይገባል ሲሉ የኪነ-ጥበብ ባለሞያዎች ጠየቁ።»
በዓለም ላይ ከፍተኛ ተጽእኖን እያሳደረ ያለዉ የኮሮና ተኅዋሲ በኢትዮጵያ በተለይ በኪነ-ጥበቡ ዘርፍ በማኅበረሰብ ጉዳይ ላይ የሚሰሩ ዜጎችን ለችግር፤ ለረሃብ፤ ብሎም አብዛኞቹን ያለመኖርያ ቤት እንዳያስቀር እያሰጋ ነዉ። ትያትር ፊልም ፤ ሙዚቀኞች ተወዛዋዦች ፤ የሥነ- ግጥም ምሽት፤ የመነባንብ ምሽት፤ የጃዥ ሙዚቃ ምሽት፤ የባህል እና የተለያዩ የመዝናኛ መድረኮች ለአብዛኛዉ ባለሞያ እና ባለተሰጦዎች የመኖርያ ምንጭ ፤ የእለት ጉርስ ማግኛ የመኖርያ ቤት ክራይ መክፈያ፤ ገንዘብ የማግኛ መድረክ ናቸዉ። በሌላ በኩል እነዚህ መድረኮች ለማኅበረሰቡ ፤ የመዝናኛ የዕዉቀት መገብያ ፤ የአገር የቀየ ጉዳይ መነጋገርያ ፤ መወያያ ሃሳብ ማመንጫ እና መለዋወጫ መድረክም ናቸዉ። እናም ኪነ-ጥበባቱን ፊት ለፊት መጥቶ አይጣላቸዉ እንጂ ድምፁን አጥፍቶ የኪነ-ጥበብ ባለሞያዎችን ሥራ እያቀጨጨ እነሱንም እየገደለ ነዉ። መፍትሄዉ ምን ይሆን ? በፊልም ስራ አዋቂዉ ታሪኩ ደሳለኝ በዚህ ጉዳይ ላይ ጥናት ጀምሮአል። አንጋፋዉ የኪነ-ጥበብ ሰዉ ደበበ እሸቱ ፤ የመንግሥት ተቀጣሪ የሆንን አርቲስቶች ከምናገኘዉ ገንዘብ አዋተን በጣም የተቸገሩትን ብንረዳስ የሚል ሃሳብ ሰጥቶአል። አሁን የመረዳጃ ጊዜ ነዉም ብሎአል። ይሁንና ይላል አርቲስት ደበበ እሸቱ ጠንካራ ማኅበር አለመኖሩ በየጊዜዉ የሚቋቋመዉ ማኅበር በመፍረሱ መሆኑን በቁጭት ይናገራል ። አርቲስት ደበበ እሸቱ ልጆቻችን ከዚህ ከኛ ችግር ሊማሩ ይገባል ሲልም ያስጠነቅቃል። የተዉኔት ደራሲ ተዋናይና ዳይሬክተር መዓዛ ወርቁ ፤ ኮሮና ወዲህ ኮሮና ወድያ ሰዉ እስኪሞት ስለማይጠብቅ ለእረት ጉርሱ የሚሆን ነገር ለመስራት መዉጣቱ አይቀሪነዉ ብላለች። ሙሉ ጥንቅሩን የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን እንዲያደምዙ እንጋብዛለን
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሐመድ