የኢትዮጵያ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች በደል በጅቡቲ
ማክሰኞ፣ ጳጉሜን 2 2013ከጅቡቲ ወደብ ወደ ኢትዮጵያ የተለያዩ ዕቃዎችን የሚያጓጉዙ የከባድ መኪና አሽከርካሪዎች ከድሬደዋ ወደ ጅቡቲ ለመግባት ኬላ ላይ በሚገጥማቸው እንግልት መቸገራቸውን ለዶይቸ ቬሌ ገለጡ። ቅሬታ አቅራቢዎቹ የሚመለከተው አካል መፍትኄ እንዲፈልግም ጠይቀዋል። በመንገዱ ላይ በሚገኘው ኬላ ለተፈጠረው ችግር የፍተሻ ሠራተኞች በአግባቡ አለመሥራት እንደምክንያት ተጠቅሷል። ከዚያ ባለፈም በአፋር እና ሶማሌ ክልል አዋሳኝ አካባቢዎች በተፈጠረው ግጭት ሳቢያ በርካታ አሽከርካሪዎች የአዋሽ ሚሌ መንገድን በመሸሽ እንደ አማራጭ በድሬደዋ በኩል ለመሄድ መገደዳቸውን አሽከርካሪዎች ጠቁመዋል።
ጭነት ለማጓጓዝ ከኢትዮጵያ ወደ ጅቡቲ የሚሄዱ ተሽከርካሪዎች በድሬደዋ በኩል ወደ ጅቡቲ ለመግባት ኬላ ላይ ከፍተኛ መጉላላት እየገጠማቸው በመሆኑ መቸገራቸውን አስተያየታቸውን ለዶይቸ ቬሌ በስልክ የሰጡ አሽከርካሪ ተናግረዋል።
አቶ ሰለሞን የተባሉ ሌላኛው አሽከርካሪ በበኩላቸው ለፍተሻ ኬላው የቆሙበት አካባቢ ምንም ዓይነት አገልግሎት የሌለበት በመሆኑ ምግብ እና ውኃ መቸገራቸውን ጠቁመዋል።አሽከርካሪዎቹ ኬላ ለማለፍ እንግልት መፈጠሩ በዕቃ ማጓጓዙ ላይ አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳለው ጠቅሰዋል።
የተፈጠረው ችግር ቀደም ሲል በአዋሽ በኩል ይገለገሉ የነበሩ ተሽከርካሪዎች በአፋር እና ሶማሌ አዋሳኝ አካባቢዎች የፈጠረውን ግጭት ተከትሎ ወደ ጅቡቲ የሚሄዱበት አማራጭ የአዋሽ ሚሌ መንገድ ላይ በተፈጠረው የሰላም ችግር መሆኑን አሽከርካሪዎች ጠቁመዋል።
ጉዳዩ የሚመለከተው የፌደራል ትራንስፖርት ሚንስቴር ሕዝብ ግንኙነት በተነሳውችግር ላይ በቂ መረጃ እንደሌላቸው ጠቅሰው ጉዳዩ የሚመለከተውን የሚንስቴሩ ኃላፊ እንድንጠይቅ ቢነግሩንም የከባድ ተሽከርካሪዎች ጉዳይ የሚመለከታቸው ኃላፊን በተንቀሳቃሽ ስልካቸው አግኝተን ምላሽ መቀበል አልቻልንም።
አሽከርካሪዎች ግን አሁን እያጋጠማቸው ያለውን ችግር መንግስት በጅቡቲ በኩል ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር መፍትሄ እንዲሰጥ ጠይቀዋል።
መሣይ ተክሉ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
ነጋሽ መሐመድ