የኢትዮጵያ እና የጀርመን የምጣኔ ሀብት መድረክ
ማክሰኞ፣ ነሐሴ 29 2010
ዓመታዊው የኢትዮጵያ እና የጀርመን የምጣኔ ሀበት መድረክ ባለፈው ሳምንት አርብ ፍራንክፈርት ጀርመን ተካሂዷል። ኢትዮጵያውያን ባለሀብቶች እና ጉዳዩ የሚመለከታቸው ባለሥልጣናት እንዲሁም የጀርመን ባለሀብቶች በተገኙበት በዚህ ጉባኤ ላይ ጥናታዊ ጽሁፎች ቀርበዋል፤ውይይትም ተካሂዷል። ኢትዮጵያ ውስጥ በአሁኑ ጊዜ መወረት የሚያስፈልግበትን ምክንያት ኢትዮጵያ ኢንቬስት ያደረጉ የጀርመን ባለሀብቶችም ልምዳቸውን አካፍለዋል። የመድረኩ ዐብይ ዓላማ በኢትዮጵያ ለመወረት ያሉትን አማራጮች እና እድሎች ለጀርመናውያን ባለሀብቶች ማስተዋወቅ መሆኑን በጀርመን የኢትዮጵያ አምባሳደር አቶ ኩማ ደመቅሳ ከኢትዮጵያ ኢንቬስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ተካ ገብረ እየሱስ ጋር ለዶቼቬለ በሰጡት ቃለ ምልልስ ተናግረዋል። እንደ አቶ ኩማ ከጉባኤው ዓላማዎች መካከል ኢትዮጵያውያን ባለሀብቶችን በኢትዮጵያ መወረት ከሚፈልጉ ጀርመናውያን ባለሀብቶች ጋር ማገናኘትም አንዱ ነው። የኢትዮጵያ ኢንቬስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ ተካ ገብረ እየሱስ እንዳሉት የጀርመን ባለሀብቶች ጀርመን በዓለም ዙርያ በምትታወቅባቸው በሃይ ቴክ ማሽነሪ፣ በግርብናው በመድሐኒት ምርት እና በመሳሰሉት ዘርፎች ኢትዮጵያ ውስጥ እንዲወርቱ ይፈለጋል። በኢትዮጵያ እና በጀርመን የምጣኔ ሀበት መድረክ ላይ የተሳተፉት ጀርመናውያን ባለሀብቶች በኢትዮጵያ የተለያዩ ተግዳሮች ቢታዩም የተሻሉ እድሎች እንዳሉ መመስከራቸውንም ተናግረዋል። ከዚህ በመነሳትም በርካታ የጀርመን ባለሀብቶች ኢትዮጵያ ውስጥ ኢንቬስት ያደርጋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅም ገልጸዋል።
ኂሩት መለሰ
አዜብ ታደሰ