የኢትዮጵያ መንግስት ጉዲፈቻን ማገዱ
ዓርብ፣ ጥር 4 2010የኢትዮጵያ መንግስት ሕጻናቱን ለጉዲፈቻ በመስጠት ፈንታ ራሱ እንክብካቤ ሊያደርግላቸዉ መፈለጉን አስታውቋል። የሕጻናት ፖሊስ አስቀድሞ ማዉጣት ግድ ይል እንደነበረ የገለጹት የሴቶችና ሕጻናት ጉዳይ ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተር አቶ አለማየሁ ማሞ ይህ ሕግ እስካሁን ለምን ሳይወጣ እንደቆየ ለዶይቼ ቬለ አስረድተዋል።
እስካሁን ድረስ በዉጭ አገር ጉዲፈቻ የሕጻናትን መብትና ደህንነት የሚያስጠብቅ ሁኔታ እንዳልነበረ የተናገሩት አቶ አለማየሁ ማህበረሰቡም ሆነ ክልሎች «አቅማቸዉን አሟጠው በመጠቀም» ሕጻናትን ሊረዱ እንደሚችሉ ስምምነት ላይ ስለተደረሰ ጉዲፈቻ እንዲቆም መወሰኑን አክለው ገልጸዋል። ሕፃናት ወደዉጭ በማደጎ መላክ ህገወጥ አሰራር እንደነበረም አቶ አለማየሁ ሳይጠቅሱ አላለፉም።
«ኢሊየን አዶፕሺንስ ኢንተርናሺናል ኢንክ» የተባለው ኢትዮጵያ ውስጥ በማደጎ ስራ ላይ ላለፉት 10 ዓመት የሰራው ድርጅት መስራችና ስራ አስኪያጅ ወይዘሮ አናቤል ኢሊየን የውጭ አገር ዜጎች ሕፃናትን በጉዲፈቻ እንዳይወስዱ መታገዱን ሲስሙ ለሕፃናቱ በማዘን እምባ እንደተናነቃቸዉ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል። በዩኤስ አሜሪካ የሚኖሩት ኢሊየን በዋነኛነት የሚጎዱት ሕፃናቱ እንጅ እኛ ወኪሎቹ አይደለንም ይላሉ።
«ይህ ለሕፃናቱ አሳዛኝ ነገር ነዉ። እኛ አንጎዳም። በጉዳቱ እኛ በሁለተኛ ደረጃ ላይ እንገኛለን። ሕፃናትን ለጉዲፈቻ ለመዉሰድ በሂደት ላይ ላሉት አመልካች ቤተሰቦች ግን አሳዛኝ ነገር ነዉ። መንግስት በሂደት ላይ የሚገኙትን የጉዲፈቻ ማመልከቻዎች እንዲጠናቀቁ እንደሚፈቅድ ተስፋ አለኝ» ይላሉ ኢሊየን።
በሂደት ላይ የሚገኙትን የጉዲፈቻ ማመልከቻዎችን በተመለከተ የሴቶችና ሕጻናት ጉዳይ ሚኒስቴር የሕዝብ ግኑኝነት ዳይሬክተር ጉዳዩ ወደፊት የሚታይ መሆኑን አመልክተዋል።
በአሜሪካ ብቻ ከ2004 ዓ.ም. ጀምሮ ከ5,500 በላይ ኢትዮጵያን ሕፃናት በማደጎ መሰጠታቸዉን ዘገባዎች ይጠቁማሉ። ለጉዲፈቻ ሕፃናትን ከተቀበሉት ዉስጥም ታዋቂዎቹ የፊልም ተዋንያን አንጄሊና ጆሊና ብራድ ፒት ይገኙበታል።
መርጋ ዮናስ
አርያም ተክሌ