1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የኢሕአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ያጸደቀው የግንባሩ ውህደት 180 አባላት ላሉት ምክር ቤትይቀርባል

ቅዳሜ፣ ኅዳር 6 2012

የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) እንዲዋሃድ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በአብላጫ ድምፅ አጸደቀ። ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴው በስድስት ተቃውሞ እና በአብላጫ ድምፅ ግንባሩን ወደ ወጥ ፓርቲነት ለመቀየር የቀረበውን ጥናት ማድደቁን የግንባሩ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አቶ ፍቃዱ ተሰማ ለብሔራዊው ቴሌቪዥን ጣቢያ ገልጸዋል። 

https://p.dw.com/p/3TAGm
Äthiopien |  Abstimmung EPRDF
ምስል EPRDF

የኢሕአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ውህደቱን ያጸደቀው ዛሬ በጠቅላይ ሚኒስቴር ጽህፈት ቤት ማካሄድ የጀመረውን ስብሰባ የአንደኛ ቀን ውሎ ሲያጠናቅቅ ነው። በዛሬው ስብሰባ ላይ የኢህአዴግ ውህደትን የተመለከተ ጥናት ቀርቦ ግልጽ ውይይት መደረጉን የጠቆሙት አቶ ፍቃዱ በስተመጨረሻ ከውሳኔ ላይ መደረሱን ገልጸዋል። 

ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው “በአጠቃላይ ብስለት፣ መደማመጥ እና ግልጽነት ያለበት ውይይት ካካሄደ በኋላ ማምሻው ላይ በስድስት ተቃውሞ በአብላጫ ድምጽ ከስምምነት ላይ ደርሷል” ብለዋል። አቶ ፍቃዱ የኢህአዴግን ውህደት የተቃወሙ አባላትን ግን በዝርዝር ከመግለጽ ተቆጥበዋል። ከሰላሳ ስድስቱ የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት መካከል ዘጠኙ የግንባሩን መዋሃድ በግልጽ ሲቃወም የቆየው የህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ (ህወሓት) አባላት ናቸው። በዛሬው የኢህአዴግ የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ የህወሓት ሊቀመንበር ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል እና ምክትላቸው ወ/ሮ ፈትለወርቅ ገብረእግዚብሔርን ጨምሮ ሌሎችም የድርጅቱ የስራ አስፈጻሚ አባላት ተገኝተዋል። የህወሓት ስራ አስፈጻሚ አባል እና የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤ  ወ/ሮ ኬሪያ ኢብራሂም በስብሰባው መክፈቻ ላይ አለመገኘታቸውን ስብሰባውን ከሚያሳዩ ምስሎች ለመመልከት ተችሏል። የኢህአዴግ አምስት አጋር ፓርቲዎች ሊቀመንበር እና ምክትሎቻቸው የዛሬውን ስብሰባ ድምጽ ሳይሰጡ ተከታትለውታል። 

Äthiopien |  Abstimmung EPRDF
ምስል EPRDF

የኢህአዴግ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ የድርጅቱን ውህደት አስመልክቶ በቀረበው ጥናት ላይ ከስምምነት ላይ ቢደርስም ቀሪ ሂደቶች መኖራቸውን አቶ ፍቃዱ ለኢትዮጵያ ቴሌቪዥን በሰጡት ቃለ ምልልስ ገልጸዋል። “ስራ አስፈጻሚው ቢያጸድቀውም ነገር ግን ወደ ምክር ቤት ነው የሚወስደው” ብለዋል። የኢህአዴግ ምክር ቤት ከአራቱ የግንባሩ መስራች ድርጅቶች የተውጣጡ 180 አባላት ያሉት ነው። ነገ በሚቀጥለው የስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ስብሰባ ለውይይት ይቀርባል የተባለው የውህድ ፓርቲው የፕሮግራም ረቂቅ ለኢሕአዴግ ምክር ቤት እንደሚመራም ጠቁመዋል። በነገው ስብሰባ ሌሎች አምስት ጉዳዮችም ውይይት እንደሚደረግባቸው አቶ ፍቃዱ ጠቅሰዋል።  

Äthiopien |  Abstimmung EPRDF
ምስል EPRDF

የቋንቋ ጉዳይ፣ ህብረ ብሔራዊ ፌደራላዊ ስርዓትን አጠናክሮ ማስቀጠል እንዲሁም የራስን ዕድል በራስ የመወሰን እና የማስተዳደር ጉዳዮች ለውይይት ከሚቀርቡት ጉዳዮች መካከል እንደሆኑ ጠቁመዋል። ሁሉንም ብሔር ብሄረሰቦች የማካተት እና ፍትሃዊ ውክልና እንዲኖራቸው ማድረግ እንደዚሁም የብሔርና ሀገራዊ ማንነትን አስታርቆ የመሄድ ጉዳይም በነገው ውይይት እንደሚነሱም አመልክተዋል። እነዚህ አምስት ጉዳዮች ውይይት ከተደረገባቸው በኋላ በሚዋሃደው ፓርቲ ፕሮግራም እና ህገ ደንብ እንደሚካተቱም አብራርተዋል። 

ተስፋለም ወልደየስ

እሸቴ በቀለ