የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነሮች ሹመት ፀደቀ
ሰኞ፣ የካቲት 14 2014ማስታወቂያ
አሥራ አንዱ የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን ኮሚሽነሮች ሹመት ዛሬ በተደረገው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሁለተኛ አስቸኳይ ጉባኤ ፀደቀ። የኮሚሽኑ ሰብሳቢዎችና አባላት ከፍተኛ የትምህርት ዝግጅት እና የሥራ ልምድ ያላቸው መሆኑን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዐፈ ጉባኤ ታገሰ ጫፎ ተናግረዋል።
በምልመላ ሂደቱ 632 ሰዎች ተጠቁመው የነበረ ሲሆን መረጣው አሳታፊ፣ ግልፅ ፣ ተአማኒነት ያለውና ገለልተኝነትን ያረጋገጠ እንዲሆን ተደርጎ መሠራቱን ገልፀዋል።
የአገራዊ ምክክር ኮሚሽኑ ኢትዮጵያ ውስጥ በልሂቃን መካከል በአገራዊ ጉዳዮች ላይ መግባባት አለመኖሩ እና በመካከላቸው ያለው አለመተማመን እና ጥርጣሬ የዴሞክራሲ የሽግግር ሂደቱን ፈታኝ በማድረጉ ማስፈለጉ መገለፁ ይታወሳል። ኮሚሽኑ መሰረታዊ በሆኑ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ለተፈጠሩ ልዩነቶች ምክንያቶችን በመለየት ገለልተኛ ናቸው ተብለው ዛሬ በተሾሙት 11 ሰዎች እየተመራ ጉዳዮቹ ላይ ውይይት እንዲካሄድባቸው ያደርጋል በዚህም መተማመን የሰፈነበት አዲስ የፖለቲካ ሥርዓት ለመፍጠር ይሰራል በሚል ውጥን ተይዟል።
ሰለሞን ሙጬ
አዜብ ታደሰ
ነጋሽ መሐመድ