ሐሙስ፣ መጋቢት 21 2009
በታሕሳስ ወር 2009 ዓ,ም ከመካከለኛዉ አሜሪካ «በፈጣን ጉዞ» ይህ የአንበጣ መንጋ መነሳቱን የሚናገሩት በኢትዮጵያ የግብርናና የተፈጥሮ ሃብት ሚንሥቴር የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ኃላፍ አቶ አለማየሁ ብርሃኑ አሁን ደግሞ ከምሥራቅ አፍራቃ ወደ ኢትዮጵያ መሸጋገሩን ለዶይቼ ቬሌ አስረድተዋል። በኢትዮጵያ በደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልል በቤንቺ ማጂ ዞን፣ በሸካ ዞንና በከፋ ዞን ዉስጥ 967 ሄክታርን የያዘ በቆሎ፣ ማሽላና ሩዝን ጨምሮ ወደ 80 የሚጠጉ የሰብል አይነቶችን የአንበጣዉ መንጋ ከጥቅም ዉጭ ማድረጉንም አቶ አለማየሁ አረጋግጠዋል።
ይህ ለአገሪቱ የመጀመርያ የተባለዉ የአንበጣ መንጋ በአንድ ጊዜ እስከ 2,000 እንቁላል መጣል እንደሚችል ያመለከቱት አቶ አለማየሁ የአካባቢዉ አርሶ አደሮች የተጎዳዉን ሰብል በመንቀልና በማቃጠል መቋቋም እንዲችሉ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮች መዘጋጀታቸዉንም ይገልጻሉ።
ኢትዮጵያ ዉስጥ የዝናብ እጥረት በተለያዩ ሀገሪቱ ክፍሎች በሰብል ምርት ላይ ባስከተለዉ ተፅዕኖ 5,6 ሚሊዮን ሰዎች ለምግብ እጥረት እንደተዳረጉ ተገልጿል። የአንበጣ መንጋዉ እያደረሰ ያለዉ ጉዳት በምግብ እጥረቱ ላይ የሚኖረዉን ተጨማር ተግዳሮት አቶ አለማየሁ እንደሚከተለዉ ያስረዳሉ።
መቀመጫዉን በታላቋ ብርታንያ ያደረገዉ Centre for Agriculture and Biosciences International (Cabi) የተሰኘዉ የጥናትተቋም በአፍሪቃ በፈጣን ጉዞ እየተስፋፋ የሚገኘዉ የአንበጣ መንጋ ወደ እስያም የመንሰራፋት አቅም እንዳለዉ ማመልከቱን ዓለም አቀፉ የዜና አዉታር ቢቢሲ ዘግቧል።
መርጋ ዮናስ
ሽዋዬ ለገሠ