የአሶሳ የኑሮ ዉድነት
ሐሙስ፣ መጋቢት 14 2015
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል አሶሳ ከተማ የምግብና የግንባታ ሸቀጦች ዋጋ አለቅጥ መጨመሩን ነዋሪዎች አስታወቁ።ባጭር ፍጥነት የጨመረዉ የሸቀጦች ዋጋ የሕዝቡን አቅም እየተፈታተነ፣ኑሮዉንም እያናጋዉ ነዉ።አሶሳ ዉስጥ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ 60 ብር የነበረው የአንድ ኪሎ ጤፍ ዋጋ ሰሞኑን 85 ብር እየተሸጠ እንደሚገኝ ነዋሪዎቹ አመልክተዋል፡፡ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ አቶ አበራ ባያታ ጤፍ የተወደደዉ ከአጎራባች ክልሎች የሚመጣ በመሆኑ ነው ይላሉ።ምርት በደበቁ ነጋዴዎች ላይም እርምጃ መወሰዱን ኃላፊዉ ገልጸዋል፡፡
በአሶሳ ከተማ ወትሮ ከነበረው በተለየ መልኩ የፍጆታ እና ግንባታ ዕቃዎች ዋጋ መጨመሩ ነዋሪዎች ገልጸዋል፡፡ በከተማው የጤፍ ዋጋ መጨመሩን ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች አስታውቋል፡፡ 20 ብር የነበረው አንድ ኪሎ ሽንኩርት 40 ብር መድረሱን፣ ስኳር በኪሎ እስከ 90 ብር ሲሆን አንድ ኩንታል ሲሚንቶ ደግሞ 2500 ብር እየተሸጠ እንደሚገኝ አብራርተዋል፡፡
በክልሉ በዘንድሮ የምርት ዘመን የተሻለ ምርት የተሰበሰበቤት ወቅት እንደነበር የክልሉ ግብርና ቢሮ ከዚህ ቀደም ይፋ አድርገዋል፡፡ ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸርም የአራት ሚሊዩን ኩንታል ብልጫ እንዳለው ተጠቁሟል፡፡ ሆኖም በክልሉ አሶሳ ከተማና አሶሳ ዞን ውስጥ በቆሎን ጨምሮ የምርት ዋጋ ጭማሪ አሳይቷል፡፡ የቁጥጥር ማነስና አሶሳን ከለሎች ስፍራዎች ጋር የሚያገናኙ መንገዶች አልፎ አልፎ መዘጋት ለምርት ዋጋ መጨመር እንደ ምክንያት እንደሆነም ነዋሪዎች ተናረግረዋል፡፡
የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ንግድና ኢንዱስትሪ ቢሮ ኃላፊ አቶ አበራ ባየታ ለዶቼቨለ በሰጡት ማብራሪያ የገበያን ዋጋ ለማረጋጋት ምክንያታዊ ያልሆነ ዋጋ ጭማሪ የሚያደረጉትን ነጋዴዎች ላይ እርምጃ ተወስደዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ በተለይም በጤፍ ላይ የተስተዋለውን የዋጋ ጭማሪ ለማስተካከል ከአጎራባች ክልሎች ምርቱ መግባቱን ጠቁመዋል፡፡ ቢሮው ባደረገው ጥናት ጤፍ በኪሎ እስከ ሰባ ብር እየተሸጠ ይገኛል ብሏል፡፡
ምክንያታዊ ያልሆነ የዋጋ ጭማሪን ለመከታተልና ለመቆጣጠር ግብረ ሀይል ተቋቁመው ወደ ስራ መግባቱ ተነግረዋል፡፡ የምርት ዋጋ ለመጨመር ሲባል ምርት የሚደብቁ ነጋዴዎችን ተቋማቸው በመለየት እርምጃ መውሰድ እንደሚቀጥልም አቶ አበራ ባየታ አስረድተዋል፡፡
ነጋሳ ደሳለኝ
ነጋሽ መሐመድ
እሸቴ በቀለ