1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የአረንጓዴ አሻራ ፕሮጀክት

ማክሰኞ፣ ሐምሌ 28 2012

ባለፈው ዓመት 4 ቢሊየን ችግኞችን ለመትከል ያቀደችው ኢትዮጵያ በአንድ ቀን 300 ሚሊየን የሚበልጡትን በመትከሏን አሳውቃለች። በዚህ ዓመትም በሀገር አቀፍ ደረጃ አምስት ቢሊየን ችግኞችን የመትከሉ እንቅስቃሴ ከተጀመረ ወራት አልፈዋል። የአረንጓዴ አሻራ ፕሮጀክቱ ሂደት ከምን ደረጃ ደርሷል?

https://p.dw.com/p/3gPqj
Äthiopien - Weltrekord im Bäume pflanzen -Symbolbild
ምስል picture-alliance/G. Fischer

«5 ቢሊየን ችግኝ በዚህ ዓመት»

በተለያዩ ጊዜያት በዘመቻ መልክም ሆነ የክረምቱን ወራት በመጣ ቁጥር ችግኝ ተከላ ኢትዮጵያ ውስጥ መከናወኑ የተለመደነው። ካለፈው ዓመት ወዲህ ደግሞ አረንጓዴ አሻራ ማሳረፍ በሚል ፕሮጀክት በቢሊየኖች የሚቆጠሩ ችግኞችን የመትከል እንቅስቃሴ ይካሄዳል። አፈርን በንፋስም ሆነ በጎርፍ ከመከላት ከመከላከል አንስቶ፣ የአየር ጠባይ ሚዛንን በመጠበቁ ረገድ ከፍተኛ ሚና እንዳላቸው የሚታመነውን ዛፎች ኅብረተሰቡን ባሳተፈ መልኩ በየአካባቢው ለመትከል የሚደረገው ጥረት ብዙዎችን አንቀሳቅሷል። ኢትዮጵያ ውስጥ ችግኝ መትከል አዲስ ባይሆንም ካለፈው ዓመት ወዲህ የሚታየው የባለሙያዎች ጥረት ብቻ ሳይሆን በመንግሥት ከፍተኛ የሥልጣን ርከን ላይ የሚገኙት ሳይቀር ትኩረት የሚሰጡት መሆኑ እንደሆነ አቶ ተፈራ ታደሰ በግብርና ሚኒስቴር የተፈጥሮ ሃብት ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ለዶቼ ቬለ ገልጸዋል። 
ዘንድሮ ለመትከል የታቀደው 5 ቢሊየን ችግኝ ሲሆን ባለፈው ዓመት 4 ቢሊየን መተከሉ ዓለም አቀፍ ትኩረት ስቧል። የዘንድሮው የችግኝ ተከላ ዝግጅት በዓመቱ መባቻ መስከረም ላይ የተጀመረና ለየአካባቢው ስነምህዳር በሚመች መልኩ እንዲሆን ጥረት መደረጉንም ከኃላፊው ተረድተናል። የዓለም የምግብና የእርሻ ደረጃ መረጃ እንደሚጠቁመው ኢትዮጵያ ውስጥ በደን  የተሸፈነው መሬት 11,2 በመቶ ቢሆን ነው። የለም አፈርን በንፋስና በውኃ የመታጠብ ስጋት ለመከላከል የተጀመረው የችግኝ ተከላ እና ለተተከሉትም የሚደረገው ክትትል አማራጭ እንደማይኖረው የዘርፉ ባለሙያዎች ያሳስባሉ። እርስዎስ አረንጓዴ አሻራዎን አሳርፈዋል? ክረምቱ አላበቃም እና ዛሬም ይችላሉ። ሙሉ ቅንብሩን ለመከታተል የድምጽ ማዕቀፉን ይጠቀሙ።

ሸዋዬ ለገሠ 

ነጋሽ መሐመድ