በምርምር የተሻሻሉ የሰብል ዝርያዎች
ረቡዕ፣ ነሐሴ 1 2011የአማራ ግብርና ምርምር ተቋም 7 አዳዲስ የሰብል ዝርያዎችን ይፋ ማድርጉን ባለፈው ሰሞን አስታውቋል።ኢንስቲትዩት ላለፉት በርካታ ዓመታት የተለያዩ የተሸሻሉ ቴክኖሎጂን በማፍለቅ ለአርሶ አደሩ ሲያደርስ መቆቱን የተቋሙ የምርምር፣ ህትመት፣ ተግባቦትና የእውቀት ስራ አመራር ተጠባባቂ ዳይሬክተር አቶ ሙሉጌታ ዓለማየሁ ለዶቼቬለ ተናግረዋል። አቶ ሙሉጌታ እንዳብራሩት ተቋሙ ምርምር ሲያደርግባቸው ከነበሩት ሰብሎች መካከል ሁለት የምግብ ሲናር፣ሁለት የጤፍ፣ አንድ የቢራ ገብስ፣ አንድ የማሽላና አንድ የዳጉሳ የተሸሻሉ ዝርያዎችን በብሔራዊ የዘር አፅዳቂ ኮሚቴ አፀድቋል። ዝርያዎቹ በተቋሙ ስር በሚገኙ የአዴትና የስሪንቃ ገግብርና ምርምር ማዕከላት ምርምር ሲደረግባቸው የቆዩ መሆናቸውንም ተቋሙ አስታውቋል የተለቀቁት ዝርያዎች የውጭ ምንዛሬን የሚያስገኙና የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥ የሚችሉ እንደሆኑም ተጠባባቂ ዳይሬክተሩ አቶ ሙሉጌታ ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል፡፡በሰብሎች ላይ የተደረገው ምርምር በአማካይ እስከ 5 ኣመታት እንደወሰደ የሚናገሩት አቶ ሙሉጌታ እነዚህ አዲስ የተገኙት የሰብል ዝርያዎች ቀደም ሲል ከነበሩት ዝርያዎች አንፃር ሲታዩ በሽታን መቋቋም የሚችሉ ምርታማነተቸውም ቀደም ሲል ከሚታወቁት ከ20 እስከ 30 ከመቶ ጭማሪ ያለው፣ በነፋስ የማይወድቁ፣ የቆላንና ደጋን የአየር ሁኔታ የሚቋቋሙ አንደሆኑ አቶ ሙሉጌታ አብራርተዋል፡፡
በአማራ ግብርና ምርምር ኢንስቲትት የአዴት ግብርና ምርምር ማዕከል የግብርና ምጣኔ ሀብትና የኤክስቴንሽን ምርምር ዳይሬክተር አቶ ይኸነው አወቀ አርሶ አደሩ አዳዲስ ዝርያዎችን ተቀብሎ እንዲጠቀምባቸው ለማድረግ ሰፊ ስራ እንደሚሰራ ጠቁመው አዳዲስ ቴክኖሎጂን ከመቀበል አኳያስ አርሶ አደሩ ያለውን ዝግጁነት በተመለከተ ሲናገሩም፣ ከምርምር የሚወጡ የተሸሻሉ ዝርያዎች ቀጥታ ገበሬው ከመጠቀሙ በፊት ያለውን ጥቅም ለአርሶ አደሩ በግልፅ ተነግሮትና አምኖበት ነው የሚወስደው ብለዋል፡፡ የግንዛቤ እጥረትና አዲስ ቴክኖሎጂን የመቃወም አዝማሚያም እንደሌለም አስረድተዋል፡፡
አቶ ስንታየሁ ሁነኛው በምእራብ ጎጃም ዞን፣ ይልማና ዴንሳ ወረዳ የሞሰቦ ቀበሌ ገበሬ ማህበር ነዋሪ ናቸው፣ ለበርካታ ዓመታት የምርምር ማዕከላት የሚያወጣቸውን የተሸሻሉ ዝርያዎች ከሚጠቀሙ አርሶ አደሮች አንዱ ናቸው፡፡ ከምርምር ማዕከሉ ምን ያህል ተጠቃሚ እንደሆኑና ቀደም ሲል ይጠቀሙበት ከነበረው ዝርያ አንፃር ምርታማነቱ ምን ያህል እንደሆነ አብራርተውልናል፡፡የአማራ ግብርና ምርምር ማእከል ከተቋቋመበት ከ1992 ጀምሮ ላለፉት 19 ዓመታት ከ600 በላይ የተሸሻሉ ዝርያዎችን፣ አንዲሁም በአፈርና ደን ልማት ምርምር፣ እንዲሁም በርካታ የማላመድ ሥራዎችን እንዳከናወነ የኢንስቲትዩቱ የምርምር፣ ህትመት፣ ተግባቦትና የእውቀት ስራ አመራር ተጠባባቂ ዳይሬክተር አቶ ሙሉጌታ ዓለማየሁ ተናግረዋል፡፡
የአማራ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት በክልሉ የተለያዩ አካባቢዎች ሰባት የምርምር ማዕከላት አሉት፡፡
አለምነው መኮንን
ኂሩት መለሰ