1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የትምህርት ማቋረጥ ስጋት በዋግኽምራ

ዓርብ፣ ጥቅምት 28 2012

በአማራ ክልል ዋግኽምራ ብሔረስብ አስተዳደር በአካባቢው ከተከሰተው ድርቅ ጋር ታያይዞ ትምህርት ቤት ምገባ ፕሮግራም በቅርብ ካልተጀመረ ትምህርት ሊቋረጥ ይችላል የሚል ስጋት እንዳደረባቸው ተማሪዎችና መምህራን ተናገሩ።

https://p.dw.com/p/3ScOo
Äthiopien Dürre in der Wagram-Zone
ምስል DW

ምዝገባው በጊዜ ካልተጀመረ ተማሪዎች ሊበተኑ ይችላሉ

የዞኑ ትምህርት መምርያ በበኩሉ ችግሩ በስፋት ተከስቶባቸዋል በተባለዉ በ 81 ቀበሌዎች ጥናት መደረጉንና እቅድ መዘጋጀቱን ሲመለክቱ የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ በበኩሉ ታህሳስ ወር ላይ የምገባ ፕሮግራም አንደሚጀምር አስታውቋል።

ሳህላ ሰየምት ወረዳ በዋግኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር በድርቅ ከተጎዱ የዞኑ ወረዳዎች አንዷ ናት። ሙሉዓለም ስምዖን በዚሁ ወረዳ የማሽሀ አጠቃላይ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ8ኛ ክፍል ተማሪ ነው። ሙሉዓለም የትምህርት ቤት ምገባ ፕሮግራም ብዙ ጊዜ በዓመቱ ማለቂያ ላይ ስለሚሆን በመማር ሂደት ላይ ተጽእኖ አንደነበረው አስታውሶ  አሁንም ካለው ድርቅ ጋር ተያይዞ ምገባው ፕሮግራሙ በጊዜ ካልተጀመረ ተማሪዎች የመበተን እድል አላቸው ብሏል። የትምህርት ቤቱ ርዕሰ መምህር አቶ አማኑኤል በሬ በበኩላቸው የምገባ ፕሮግራሙ እንዳልተጀመረ ጠቅሰው የሚዘገይ ከሆነ መቋረጡ  የማይቀር ነው ሲሉ ስጋታቸውን ለዶይቼ  ቬለ«DW» በስልክ ተናግረዋል። የሳህላ ሰየምት ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ሚሳው ፋንታዬ በስልክ ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ ካለው ወቅታዊ አንፃር የምገባ ፕሮግራም ቀድሞ እንዲጀመር ለሚመለከተው ሁሉ ቢያመለክቱም ተግባራዊ ምላሽ እንዳልተሰጠ አስረድተዋል። የድርቅ ስጋት አለባቸው  የተባለባቸዉ  81 ቀበሌዎች መለየታቸውንና ወደተግባር ለመግባት እቅድ  መዘጋጀቱን የተናገሩት የዋግኽምራ ብሔረሰብ አስተዳደር የትምህርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ሽታው አዳነ ተናግረዋል። የአማራ ክልል ትምህርት ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ይልቃል ከፋለ ተማሪዎች የተማሪዎች ትምህርት ማቋረጥ ስጋትን ለመከላከል የምገባ ፕሮግራም ከታህሳስ ወር ጀምሮ ይቀጥላል ብለዋል። በያዝነው ዓመት በብሔረሰብ አስተዳደር ዞኑ ከነበረው ዝቅተኛና የተቆራረጠ ዝናብ ምክንያት ከፍተኛ የድርቅ ችግር ተከሰቶ አጠቃላይ ካለው 600 ሺህ የዞኑ ህዝብ መካከል 126 ሺህ  ነዋሪ ለአስቸኳይ የምግብ እርዳታ መጋለጡ ታዉቋል።

 

ዓለምነው መኮንን

አዜብ ታደሰ

ነጋሽ መሃመድ