የቴሌኮም ጨረታ ውጤትና የአሜሪካ ማዕቀብ
ረቡዕ፣ ግንቦት 18 2013ማስታወቂያ
በኢትዮጵያ ውስጥ የቴሌኮም አገልግሎት ለመስጠት ጨረታ ያሻነፈው ዓለም አቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያ የተባለው የኩባንያዎች ጥምረት ሥራውን በቅርቡ ይጀምራል ተባለ። ሠራተኞችን መቅጠር መጀመሩ የተነገረለት ይሄው ጥምረት የዘርፉን አገልግሎት አሰጣጥ ጥራት በብዙ መልኩ ያሻሽላል የሚል ተስፋ ተጥሎበትል። አሜሪካ በኢትዮጵያ ላይ የጣለችው የባለሥልጣናት ቪዛ እና የኢኮኖሚ ማዕቀብ በጥምረቱ ተግባር ላይ ተፅእኖ እንደሚኖረው የገለፁት አንድ የምጣኔ ሀብት ባለሙያ ኢትዮጵያ ከአሜሪካ ጋር ተቀራርባ መሥራት እንደሚበጃት ተናግረዋል። እንደ ማሳያም አፍሪቃም ሆነ ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ ከብድርና ርዳታ ውጪ ሆነው ራሳቸውን ችለው መቆም እንደማይችሉም አጽንኦት ሰጥተዋል። ከጥምረቱ ኩባንያዎች አንዱ የሆነው ቮዳፎን በኢትዮጵያ ላይ የተጣለው ማዕቀብ ለሥራው ችግር እንደሚደቅንበት ተናግሮ የነበር ቢሆንም ጥምረቱ ትናንት ባወጣው መግለጫ ግን ሥራውን በቅርቡ እንደሚጀምር አመልክቷል። የመንግሥት የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ መርሃ ግብር አካል ነው የተባለው ይህ በቴሌኮም ዘርፉ ገበያ ላይ የውጭ ድርጅቶች እንዲገቡ የተፈቀደበት ስርዓት ብዙ የሥራ ዕድል ይፈጥራል ተብሎ ተስፋ ተጥሎበታል።
ሰሎሞን ሙጬ
ሸዋዬ ለገሠ