የተፈናቀሉ ወገኖች አቤቱታ ከትግራይ
ዓርብ፣ ነሐሴ 3 2011በትግራይ ከ2008 ዓ.ም ጀምሮ የተፈናቀሉ ከ111 ሺህ በላይ እርዳታ ፈላጊ ተፈናቃዮች እንዳሉ የክልሉ የሠራተኞች እና ማኅበራዊ ጉዳይ ቢሮ መረጃ ያመለክታል።
ያነጋገርናቸው በመቐለ የተፈናቃዮች መጠለያ የሚኖሩ እርዳታ ፈላጊ ዜጎች እንደሚሉት በየወሩ መንግሥት ከሚሰጣቸው 15 ኪሎ ስንዴ ውጪ የሚደረግላቸው ተጨማሪ ድጋፍ ባለመኖሩ ችግር ላይ ናቸው። ወደ ነበሩበት አካባቢ ዳግም ለመመለስ የደህንነት ስጋት እንዳለባቸው በመግለፅ መመለስ እንደማይፈልጉ የሚናገሩት ተፈናቃዮቹ ዘላቂ የማቋቋምያ ድጋፍ አግኝተው ሠርተው መኖር እንደሚሹ ይገልጻሉ። ባለፊት አራት ዓመታት ከኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ተፈናቅለው ወደ ትግራይ የመጡ ተፈናቃዮች ለማቋቋም 1 ነጥብ 5 ቢልዮን ብር እንደሚያስፈልግ ጥናቶች ያስረዳሉ። ይሁንና የክልሉ መንግስት ተፈናቃዮችን ለማገዝ ባደረገው ገቢ ማሰባሰብ የተገኘው ገንዘብ ከ100 ሚልዮን ብር የማያልፍ መሆኑ በትግራይ ክልል ሠራተኞችና ማሕበራዊ ጉዳይ ቢሮ የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ጉዳይ ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ ሙልጌታ ኃይለ ለዶይቸ ቨለ DW ተናግረዋል።
የፌደራል መንግሥት የክልሉ ተፈናቃዮች ለማቋቋም ለቀረበለት የድጋፍ ጥሪ እስካሁን ምላሽ አለመስጠቱም የሀገር ውስጥ ተፈናቃዮች ጉዳይ ጽሕፈት ቤት ገልጿል። በዚህም የክልሉ መንግሥት መፍትሔ ያደረገው «እጅግ በጣም የተቸገሩ የተባሉ ተፈናቃዮች ተመርጠው እነርሱን ብቻ መደገፍና ማቋቋም» መሆኑ የጠቆሙት አቶ ሙልጌታ ሌሎቹ የማሰናበት ስራ ይሰራል ብለዋል፡፡
ብሔራዊ አደጋ ስጋት ሥራ አመራር የተባለ የኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት ኮምሽን ባለፉት ወራት 2,1 ሚልዮን የሀገሪቱ ተፈናቃዮች ወደ ቅያቸው መመለሰ ሰሞኑን ገልፅዋል።
ሚሊየን ኃይለ ሥላሴ
ሸዋዬ ለገሠ
ኂሩት መለሰ