1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የተዛመተው የደን ቃጠሎ በኢትዮጵያ

ማክሰኞ፣ መጋቢት 21 2013

ኢትዮጵያ ውስጥ ከቅርብ ሳምንታት ወዲህ በተለያዩ የደን አካባቢዎችና ይዞታዎች ላይ የእሳት ቃጠሎ ተከስቷል። አንዳንዱ እሳት በቁጥጥር ስር ሲውል ያልበረደም መኖሩ ይነገራል። እሳቱ ከተነሳባቸው አካባቢዎች አንዳንዶቹ በመንግሥት ጥበቃ የሚደረግላቸው መሆናቸውም ተሰምቷል።

https://p.dw.com/p/3rOBe
Grenzstreit zwischen Äthiopien und Sudan I Metema Stadt
ምስል Alemenew Mekonnen/DW

«መንስኤው ተፈጥሯዊና ሰው ሠራሽ ነው»

በኢትዮጵያ ከሳምንታት ወዲህ መንግሥት ከልሎ ሕጋዊ ጥበቃ በሚያደርግላቸው ብሔራዊ ፓርኮች እና የተለያየ ይዘትና መጠን ባላቸው ደኖች ላይ የእሳት አደጋ እየተቀሰቀሰ ከፍተኛ የሚባል የሥነ ምህዳር ውድመት እያስከተለ መሆኑ ታውቋል። ከሰሞኑ ብቻ በአማራ ፣ ኦሮምያ ፣ አፋርና ደቡብ ብ/ብ/ሕ/ ክልል ውስጥ በተለያዩ ሥፍራዎች ጉዳት ያደረሰ፤ በአንዳንዶቹ ቦታዎች ላይ እስካሁንም ያልጠፋ የእሳት ቃጠሎ አደጋዎች በተፈጥሮ ሀብት ላይ ጉዳት አድርሷል፣ እያደረሰም ይገኛል። የእሳት አደጋዎቹ ያደረሱት የጉዳት መጠን እስካሁን ታውቆ ይፋ ባይደረግም በተፈጥሮ የሥነ ምህዳር ጤንነት ላይ ግን ሚዛን የሚያዛባ ችግር አስከትለዋል። ያለው በረሃማነትና ከፍተኛ የሙቀት መጠን ፣ በአርብቶ እና አርሶ አደሮች የተሻለ የግጦሽ ሳር ፍለጋን በማሰብ በሳር ላይ የሚለቀቀው እሳት ከቁጥጥር ውጪ ማለፍ፣ በሕገወጥ ሁኔታ ማር ለመቁረጥና ንብ ለማነብ ብሎም ከሰል ለማክሰል የሚደረግ ጥረት ላይ የሚያመልጥ እሳት ብሎም የጥንቃቄ ጉድለት ለእሳት አደጋዎቹ መነሻ ተደርገው ይወሰዳሉ።

ሰሎሞን ሙጬ

ሸዋዬ ለገሠ