የቤሕነን መሪ በአሶሳ በቁጥጥር ሥር ዋሉ ተባለ
ዓርብ፣ ታኅሣሥ 5 2011ማስታወቂያ
ከኤርትራ የተመለሰው የቤኒሻንጉል ሕዝቦች ነፃነት ንቅናቄ መሪ በትናንትናው ዕለት በአሶሳ ከተማ በጸጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ሥር መዋላቸውን የአይን እማኞች ተናገሩ። አቶ አብዱልዋሀብ መሀዲ የተባሉት የንቅናቄው መሪ ለምን በቁጥጥር ሥር እንደዋሉ የታወቀ ነገር የለም። የአይን እማኞች ግን ባለፈው ሰኔ በአሶሳ ከተማ ተቀስቅሶ በነበረው ግጭት ሳቢያ በጸጥታ ኃይሎች ክትትል ውስጥ እንደነበሩ ይናገራሉ። የኢትዮጵያ መንግሥት እስካሁን በጉዳዩ ላይ የሰጠው ማብራሪያ የለም።
አቶ አብዱልዋሀብ በቁጥጥር ለማዋል የጸጥታ ኃይሎች ባደረጉት ጥረት ግለሰቡ ለመሸሽ ሲሞክሩ መኪናቸው በደረሰበት ግጭት በአካባቢው በነበሩ ሰዎች ላይ ጉዳት መድረሱን የአይን እማኝ ለDW ተናግረዋል። የአካባቢው ነዋሪዎች በክልሉ ከተፈጠሩ የጸጥታ ቀውሶች ጀርባ የአብዱልዋሀብ መሀዲ እጅ አለበት ሲሉ ይከሳሉ።
ቤሕነን ከመሸገበት ኤርትራ በይቅርታ ከመመለሱ በፊት አባላቱ "የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልን ለመገንጠል የሽብርተኝነት ድርጊት ፈጽመዋል" የሚል ክስ በኢትዮጵያ መንግሥት ቀርቦባቸው ነበር። አቶ አብዱልዋሀብ በቁጥጥር ሥር ሲውሉ የተመለከቱ የአሶሳ ከተማ ነዋሪ በወቅቱ የጥይት ተኩስ እንደነበር ገልጸዋል። የአይን እማኙን እሸቴ በቀለ በስልክ አነጋግሯቸዋል።
እሸቴ በቀለ
አዜብ ታደሰ