የቀጠለው የሕክምና ባለሙያዎች ተቃውሞ
ዓርብ፣ ግንቦት 9 2011በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ የቅዱስ ጳውሎስ ሆስፒታል ሀኪሞች በግቢያቸው ተሰባስበው ቅሬታቸውን ለመግለፅ ሞክረዋል። በተመሳሳይም በአክሱም ከተማ የሚገኙ የሕክምና ባለሙያዎች በጥቅማጥቅምና በሕክምና ስርዓቱ አሉ ባሉዋቸው ችግሮች ዙርያ ተቃውሞ ማሰማታቸውን የመቀሌው ዘጋቢያችን የላከልን ዘገባ ያስረዳል። የአክሱም ከተማ አስተዳደር የሕክምና ባለሙያዋቹ በከተማ ተዘዋውረው ተቃውሟቸውን እንዳይገልፁ በመከልከሉ ከሚሰሩበት ሆስፒታል መውጣት አልቻሉም። አስተዳደሩ ሰልፈኞቹ ወደ ከተማው ወጥተው ድምፃቸው እንዳያሰሙ የከለከለው «ተደራራቢ መርሐ ግብሮች በከተማዋ እየተካሄዱ በመሆኑ በቂ የፀጥታ ኃይል መመደብ ስላልቻልኩ ነው» ብሏል። ሀኪሞቹ ሥራ የማቆም ፍላጎት እንደሌላቸው በመግለፅ ድምፃቸውን ያሰሙት በዕረፍት ሰዓታቸው መሆኑ ተናግረዋል፡፡
በአክሱም ከተማ ከተደረገው የሕክምና ባለሙያዎች የተቃውሞ ሰልፍ በተጨማሪ በመቐለ ዓይደር ሪፈራል ሆስፒታል ቅጥር ግቢ እንዲሁም በዓዲግራት ሆስፒታል የተቃውሞ ሰልፎች ተካሂደዋል። በሰልፎቹ «የሐኪሞች ድምፅ ይሰማ፣ ባዶ ሕንፃ ሆስፒታል አይባልም፣ ማስፈራራትና ዓፈና ይቁም» የሚሉና ሌሎች መፈክሮች በሕክምና ባለሙያዎቹ ተስተጋብተዋል። ከዚህ በተጨማሪ የትግራይ ክልል ምክትል ርእሰ መስተዳድር ዶክተር ደብረፅዮን ገብረ ሚካኤል እና የጤና ሚኒስቴር ሚኒስቴር ደኤታ ወይዘሮ ሳሃራላ ዓብዱላሂ በመቐለ ከትግራይ የጤና ባለሙያዎች ጋር ተወያይተዋል።
ዮሐንስ ገብረ እግዚአብሔር/ ሚሊየን ኃይለ ሥላሴ
ሸዋዬ ለገሠ
ኂሩት መለሰ