1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የሲሚንቶ አቅርቦት ችግር በድሬዳዋ

ሐሙስ፣ ሰኔ 24 2013

ዶይቸ ቬለ ሁለት የሲሚንቶ አምራች ኢንደስትሪዎች ባሉባት ከተማ ያጋጠመው ችግር የምርት አቅርቦት ለመሆኑ መረጃ ለመውሰድ ያነጋገራቸው የድሬደዋ ናሽናል ሲሚንቶ አ.ማ ምክትል ስራ አስፈፃሚ አቶ አብዱሰመድ መሀመድ ፋብሪካው የሚያመርተውን ምርት በአግባቡ ለአከፋፋዮች እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።

https://p.dw.com/p/3vu6V
Äthiopien Dire Dawa City
ምስል DW/Y. Gebreegziabher

የሲሚንቶ አቅርቦት ችግር በድሬዳዋ

ለሲሚንቶ ምርት አመቺ በተባለችው ድሬደዋ የሲሚንቶ አቅርቦቱ ጤነኛ ባለመሆኑ መቸገራቸውን በዘርፉ ንግድ የተሰማሩ ቸርቻሪዎች ለዶይቸ ቬለ ተናግረዋል፡፡ መንገስት በበኩሉ የተፈጠረውን ችግር ተቀብሎ ለማስተካከል እንደሚሰራ አስታውቋል።በድሬደዋ በኮንስትራክሽን ግብዓቶች ምርት አቅራቢነት ስራ ላይ የተሰማሩት ዶ/ር ተካልኝ ፀጋሁን ለዶይቸ ቬለ  “ወደ ህገ ወጥ ንግድ ወይም ኮንትሮባንድ በተሸጋገረው የሲሚንቶ ገበያ ፣ስራ መስራት አስቸጋሪ በመሆኑ ሰራተኞቻቸውን መበተናቸውን” ተናግረዋል፡፡

በሲሚንቶ ችርቻሮ ንግድ ላይ የተሰማሩት አቶ ናስር ርጋ በበኩላቸው በሲሚንቶ አቅርቦቱ ላይ ያጋጠመው ችግር የዋጋ ንረት መፍጠሩን ገልጠው መፍትሄ ለማግኘት ወደ ሚመለከተው የመንግስት አካል ብንሄድም መፍትሄ እየተገኘ አይደለም ብለዋል፡፡

ዶይቸ ቬለ ሁለት የሲሚንቶ አምራች ኢንደስትሪዎች ባሉባት ከተማ ያጋጠመው ችግር የምርት አቅርቦት ለመሆኑ መረጃ ለመውሰድ ያነጋገራቸው የድሬደዋ ናሽናል ሲሚንቶ አ.ማ ምክትል ስራ አስፈፃሚ አቶ አብዱሰመድ መሀመድ ፋብሪካው የሚያመርተውን ምርት በአግባቡ ለአከፋፋዮች እየሰጠ መሆኑን ተናግረዋል።ናሽናል ሲሚንቶ በአቅርቦት ላይ ያሉ ችግሮችን ለመፍታት ከመስተዳድሩ ጋር የተያየ ተግባር እያከናወኑ መሆኑን የጠቆሙት ምክትል ስራ አስፈፃሚው በአከፋፋዮች የሚፈጠር ችግር ካለም አስተዳደሩ በሚሰጠው መመርያ መሰረት እየሰሩ መሆናቸውን አስረድተዋል።የድሬደዋ አስተዳደር ንግድ ፣ ኢንደስትሪ እና ኢንቨስትመንት ቢሮ ምክትል ሓላፊ አቶ አብዲ ሙክታር ያጋጠመው ችግር ትክክለኛ መሆኑን ጠቅሰው በአጭር ጊዜ መፍትሄ ለመስጠት እየሰራን ነው ብለዋል።በድሬደዋ ላጋጠመው የሲሚንቶ አቅርቦት ችግር መሰረታዊው ጉዳይ የቁጥጥር ስርዓቱ ነው የሚለው አስተያየት የብዙዎቹ አከፋፋዮች ነው፡፡

መሳይ ተክሉ 

ኂሩት መለሰ