1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

የህዳሴ ግድብ ተደራዳሪዎች ልዩነት በአጭር ጊዜ ይጠባል ማለት አስቸጋሪ ነው-ፈቂ አሕመድ

ሰኞ፣ ሰኔ 8 2012

የግብጽ የውኃ ሐብትና መስኖ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ "እየተካሔደ በሚገኘው ድርድር ስምምነት ይደረሳል የሚል ተስፋ የለኝም" ብለዋል። ኢትዮጵያ እንደምትለው ድርድሩ ባይሰምር እንኳ የማይሳካው ግብጽ ኢትዮጵያና የላይኛው ተፋሰስ አገራትን ተፈጥሯዊና ፍትሐዊ መብቶች የሚከለክለውን የቅኝ ግዛት ዘመን ስምምነት ለማስቀጠል ድርቅ በማለቷ ነው

https://p.dw.com/p/3dnbc
Äthiopien Luftbild Grand-Ethiopian-Renaissance-Talsperre
ምስል DW/Negassa Desalegen

የህዳሴ ግድብ ተደራዳሪዎች ልዩነት በአጭር ጊዜ ይጠባል ማለት አስቸጋሪ ነው-ፈቂ አሕመድ

ኢትዮጵያ እና ግብጽ በህዳሴ ግድብ ላይ በኢንተርኔት እየተደራደሩ በተናጠል ልዩነቶቻቸው መካረሩን የሚጠቁም መግለጫ ያወጣሉ። በታላቁ የኅዳሴ ግድብ ላይ በሚደረገው የሶስትዮሽ ድርድር ኢትዮጵያ "ግትር አቋም" ይዛለች ስትል ግብጽ ባለፈው ቅዳሜ ወንጅላለች። የግብጽ የውኃ ሐብት እና መስኖ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ መሐመድ አል-ሴባይ ባወጡት መግለጫ "እየተካሔደ በሚገኘው ድርድር ከአንዳች ስምምነት ይደረሳል የሚል ተስፋ የለኝም" ብለዋል። 

ኢትዮጵያ በበኩሏ ትናንት ባወጣችው መግለጫ ድርድሩ ፍሬ አልባ ሊሆን ይችላል የሚለውን የግብጽ አቋም አጣጥላለች።  የኢትዮጵያ የውኃ፣ የመስኖና የኢነርጂ ሚኒስቴር ድርድሩ ውጤት አልባ ከሆነ ተጠያቂዋ ግብጽ ነች ብሏል። ሚኒስቴሩ ድርድሩ ባይሰምር እንኳ የማይሳካው ግብጽ ኢትዮጵያ እና የላይኛው ተፋሰስ አገራትን ተፈጥሯዊ እና ፍትሐዊ መብቶች የሚከለክለውን የቅኝ ግዛት ዘመን ስምምነት ለማስቀጠል ድርቅ በማለቷ ነው ብሏል። 

እንደ አዲስ የተጀመረውን ድርድር አሜሪካ፣ የአውሮፓ ኅብረት እና ደቡብ አፍሪካ በታዛቢነት ይሳተፉበታል። ኢትዮጵያ፣ ግብጽ እና ሱዳን የታዛቢዎቹ ሚና ምን ይሁን በሚለው ጉዳይ ላይ እንዳልተስማሙ ኢትዮጵያ አስታውቃለች።

ኢትዮጵያ፣ ግብጽ እና ሱዳን ተቋርጦ የነበረውን ድርድር በኢንተርኔት አማካኝነት የጀመሩት ማክሰኞ ሰኔ 2 ቀን 2012 ዓ.ም. ነበር። ኢትዮጵያ በመጪው ሐምሌ ግድቡን ውኃ መሙላት ከመጀመሯ በፊት ሶስቱ አገሮች ከአንዳች ስምምነት ይደርሳሉ ተብሎ ቢጠበቅም የሚሳካ አይመስልም።  የምስራቅ ናይል ቴክኒካል አህጉራዊ ጽህፈት ቤት ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ፈቂ አህመድ ነጋሽ እንደሚሉት የህዳሴ ግድብ ተደራዳሪዎች ልዩነት በአጭር ጊዜ ይጠባል ማለት አስቸጋሪ ነው። ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ አነጋግሯቸዋል።


ጌታቸው ተድላ ኃይለ ጊዮርጊስ
ነጋሽ መሐመድ