የ8 ዓመት ልጅ በባቡር ተገጨ፤ ኤርትራዊዉ ተጠርጥሮአል
ሰኞ፣ ሐምሌ 22 2011ማስታወቂያ
በፍራንክፈርት ዋና የባቡር ጣብያ ከስምንት ዓመት ልጅዋ ጋር ሆና ባቡር ስትጠብቅ የነበረች አንዲት ሴት በአንድ ሰዉ ተገፍትራ የስምንት ዓመት ልጅዋ በፈጣን ባቡር ሲገጭ እስዋ ግን ለጥቂት መትረፍዋን ፖሊስ አመለከተ። ሲቲቱ የምን ሃገር ዜጋ እንደሆነች ባይገለፅም ገፍታሪዉ ተጠርጣሪ ኤርትራዊ እንደሆን ተመልክቶአል። ይህ ሁሉ የሆነዉ ዛሬ ረፋዱ ላይ ሲሆን የፍራንክፈርት ፖሊስ እስካሆን የሰጠዉ ዝርዝር መግለጫ የለም። የ 40 ዓመቲቱ ሴት ወደ ሆስፒታል የተወሰደች ሲሆን፤ ገፍታሪዉ ተጠርጣሪ ባቡር ይዞ አምልጦ በቀጣይ የባቡር ማቆምያ ላይ ሰዎች ይዘዉ ለፖሊስ እንዳስረከቡት ተመልክቶአል። በወጣዉ የመጀመርያ መረጃ መሰረት በሴቲቱና በተጠርጣሪ ወንጀለኛ መካከል ምንም አይነት ትዉዉቅ የለም። ገፍታሪ የተባለዉ ተጠርጣሪ ኤርትራዊ ሌላ አንድ ሰዉን እንዲሁ ለመገፍተር ሞክሮ ነበር ተብሎአል። አደጋዉ በደረሰበት የባቡር መስመር ላይ ለሰዓታት ስራ ቆምም ነበር።
አዜብ ታደሰ
እሸቴ በቀለ