1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዛሬም የሚያሳስበው የTB ስርጭት

ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 12 2013

የዓለም የጤና ድርጅት አደገኛ ተላላፊ በሽታ ከሚባሉት ግንባር ቀደም መሆኑን ይገልጻል TB። በየዓመቱም ከአንድ ሚሊየን የሚበልጡ ሰዎችን ሕይወት TB እንደሚቀጥፍም መረጃው ያመለክታል። ኢትዮጵያም ውስጥ በዓመት ከ150 ሺህ ሰዎች በላይ በዚሁ በሽታ ሕይወታቸው ያልፋል።

https://p.dw.com/p/3sI4S
Mycobacterium Tuberculosis
ምስል picture-alliance/BSIP/NIAID

«TB ከተስፋፋባቸው 30 ሃገራት ኢትዮጵያ አንዷ ናት»

ባለፈው ጎርጎሪዮሳዊ ዓመት ዓለምን ያዳረሰው የኮቪድ 19 ወረርሽኝ አንድ ሚሊየን ሰዎችን መፍጀቱ ብዙዎችን አስደንጓጧል። መረጃዎች እንደሚያሳዩት ግን ለበርካታ አስርት ዓመታት በየዓመቱ በTB ምክንያት ከ1,5 እስከ ሁለት ሚሊየን የሚሆኑ ሰዎች ያልቃሉ።  ኢትዮጵያ TB በሰፊው ተስፋፍቶ ከሚገኝባቸው 30 ሃገራት አንዷ ናት። የጤና ሚኒስቴር የTBን ስርጭት ለመግታት ጊዜው አሁን መሆኑን ከሳምንታት በፊት የዓለም የTB ቀን ሲታሰብ ይፋ አድርጓል። ዶክተር አንዳርጋቸው ኩምሳ በፌደራል ጤና ሚኒስቴር መድኃኒት የተላመደ TB ከፍተኛ አማካሪ ናቸው። ኢትዮጵያ የTB ተሐዋሲ በከፍተኛ ደረጃ ከተሰራጨባቸው 30 ሃገራት አንዷ ናት ሲባል በተጨባጭ ያለው ይዞታ ምን እንደሚመስል እንዲህ ያስረዳሉ።

«የበሽታው ስርጭት ከፍተኛ ነው ስንል አሁን ያለው የTB በሽታ ስርጭት ሁኔታ ከ100 ሺህ 140 ሰዎች ላይ TB እንዳለባቸው ነው የሚያሳየው።  ከዚያም አልፎ ግን በአሁኑ ጊዜ በኢትዮጵያ ከእያንዳንዱ መቶ ሺህ ሰው ውስጥ 19 ሰዎች በTB ምክንያት ይሞታሉ። ይኼ ማለት በዓመት ውስጥ ቁጥሩ የሚያሳየው 21 ሺህ አካባቢ በTB ብቻ ይሞታሉ፤ ይኼ ማለት በየአንዳንዱ ቀን ወደ 57 ሰዎች በTB ይሞታሉ ማለት ነው።»

Tuberkulose in Indien Krankenhaus in Howrah Medikamente Tabletten Medizin
ምስል picture-alliance

ባለሙያው እንደሚሉት ቀደም ብሎ በኢትዮጵያ የነበረው የTB በሽታ ስርጭት መጠኑ ከጎርጎሪዮሳዊው 2015 ዓ,ም ወዲህ ቀንሶ የታየ ለውጥ መሆኑ ነው። ቀድሞ ከነበረውም ወደ ከ20 እስከ 27 በመቶ መቀነሱን ቢገልጹም አሁንም ቁጥሩ በጣም ትልቅ መሆኑን አጽንኦት ሰጥተዋል። ከዚህም ሌላ መድኃኒት የተላመደው የTB በሽታን አስመልክቶም ኢትዮጵያ አሁንም ችግሩ በሰፊው ከሚታይባቸው ሃገራት አንዷ መሆኗንም ገልጸዋል።

TB ለመላው ዓለም የራስ ምታት ሆኖ የከረመ አደገኛ ተሐዋሲ ቢሆንም በተለይ በሕንድ፤ ኢንዶኔዢያ፤ ደቡብ አፍሪቃ፤ ባንግላዴሽ፣ ቻይና፤ ፊሊፒንስ፣ ናይጀሪያ፣ ኢትዮጵያ እና ፓኪስታን እጅግ የተስፋፋ በሽታ መሆኑን የዓለም የጤና ድርጅት ያመለክታል። እነዚህ ሃገራት ከመላው ዓለም ሁለት ሶስተኛ የሚሆነው የበሽታውን ስርጭት የተሸከሙ መሆናቸውን መረጃዎች ያሳያሉ።

ሙሉ ቅንብሩን ከድምጽ ዘገባው ያድምጡ፤

ሸዋዬ ለገሠ

እሸቴ በቀለ