1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዉይይት፤ አዲሱ 2011 ዓመት ለኢትዮጵያ ፖለቲካ ተስፋ?

እሑድ፣ ጳጉሜን 4 2010

የሚጠናቀቀዉ የኢትዮጵያ 2010 ዓመት በሃገሪቱ የ 27 ዓመታት ታሪክ የተለየ ስፍራ ስፍራ የሚሰጠዉ ነዉ። ከዓመታት በፊት የጀመረዉ ሕዝባዊ ተቃዉሞ እና አመፅ የተባባሰበት፤ ሃገሪቱ ሁለት ጊዜ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስር የወደቀችበት፤ በሌላ በኩል በጠ/ሚ የሚመራዉ አዲስ መንግሥት አዲስ ተስፋን ያሰነቀበት ነበር።

https://p.dw.com/p/34a5O
Neujahrfest 2011 Äthiopien
ምስል Mekeit Teka

«ሕገ-መንግሥቱ ዳግም ሊጤን፤ የሕግ የበላይነት ሊሰፍን ይገባል»

የምንሸኘዉ የኢትዮጵያ 2010 ዓመት በሃገሪቱ የ 27 ዓመታት ታሪክ የተለየ ስፍራ ስፍራ የሚሰጠዉ ነዉ። ከዓመታት በፊት የጀመረዉ ሕዝባዊ ተቃዉሞ እና አመፅ የተባባሰበት፤ በሃገሪቱ ለሁለተኛ ጊዜ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እንድትተዳደር የተወሰነበት፤ «ሕዝቡ ሃገሪቱ ወዴት አቅጣጫ እየሄደች ነዉ?» ሲል ብዙ ያሰበና የተጨነቀበት ነበር። በየአካባቢዉ በሚነሱ አመፅና ተቃዉሞዎች ምክንያት ብዙ ሰዎች ሕይወታቸዉን ያጡበት የሕዝቡ የመንቀሳቀስ መብት የተገደበበት የሃገሪቱ ምጣኔ ሃብትም አሳሳቢ ደረጃ ላይ የደረሰበት ጊዜ ነበር። ይሁንና ዓመቱ ሲጋመስ ባልተጠበቀ ሁኔታ የቀድሞዉ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማርያም ደስአለኝ በፈቃዳቸዉን ስልጣናቸዉን ለቀዋል። ባለፈዉ መጋቢት 24 ዶ/ር ዐብይ አሕመድ የኢህአዴግ ሊቀመንበር እና የሃገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነዉ ተሰይመዋል። ጠ/ሚ ዐብይ አሕመድ ስልጣን ከያዙ ወዲህ ላለፉት አራት ወራት በኢትዮጵያ በየመስኩ የታየዉ አወንታዊ ለዉጥ ተስፋን ያሰነቀና ልዩ ትኩረት የሚሰጠዉ ነዉ። የኢትዮ ኤርትራ የሰላም ስምምነት፤ በብዙ ሺህ የሚቆጠቱ እስረኞችን መልቀቅ፤  የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እና በተለያዩ መገናኛ ዘዴዎች ላይ የተጣለዉ እገዳ ማንሳት፤ ሠዎችን በነፃነት የመቃወም መብት መጠበቅ፤ በተለያየ ጎራ በዉጭ ሃገራት በትጥቅም ሆነ በሰላማዊ ትግል የነበሩና በአሸባሪነት የተወነጀሉ የፖለቲካ ፓርቲዎችም ሆኑ ዜጎች የተላለፈዉን ጥሪ እና የምህረት አዋጅ በመጠቀም ወደ ሃገር እየገቡ መሆናቸዉ ይገኝበታል። ይህ ሁሉ በሃገሪቱ አዲስ ተስፋን ፈንጥቆአል። ከዚህ በተጨማሪ በሃገሪቱ ለረጅም ጊዜ በተለያየ ሥልጣን ላይ የነበሩ በተለይም የደህንነት እና የጦር ኃይሉን ይመሩ የነበሩ ከፍተኛ ባለሥልጣናት በማንሳቱ ሕዝቡ ከፍተኛ ደስታ ተሰምቶት ድጋፍም ሰጥቶታል። የዶ/ር ዐብይ መንግሥት ሌሎች በርካታ በሕዝብ ዘንድ ድጋፍ ያስገኘለት ርምጃዎችን ወስዶአል። ሆኖም ከዚሁ ሁሉ ፈጣን ለዉጥ ጎን ለጎን ዓመቱ ግጭት ግድያ ዝርፍያ ሁከት እናም በአንዳንድ የሃገሪቱ ክፍል ከመቼዉም ጊዜ በበለጠ የሕዝብ መፈናቀል የታየበት ዓመት ነበር። በዚህ ዉይይታችን ከቀናት በኃላ የምንሸኘዉን 2010 ዓመትን ወደ ኋላ እየቃኘን በአዲሱ በ 2011 ዓመት ምን መሻሻል፤ መሰራት እንዳለብን እና ተስፋዉን እናያለን።  የዉይይቱ ተሳታፊዎች ፤ ወጣት ወይንሸት ሞላ ፖለቲከኛ፤ አቶ ዱባለ ገበየሁ በአዋሳ ዩንቨርስቲ የሥነ ሰብዕ መምህር፤ አቶ አምዶም ገብረስላሴ የአረና ትግራይ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ፤ አበበ ገላዉ ፤ የሰብዓዊ መብት አቀንቃኝ እና ጋዜጠኛ ናቸዉ። ተወያዮች በዉይይቱ ሃሳባቸዉን በመስጠት በመሳተፋቸዉ በ «DW» ስም እያመሰገንን፤ ሙሉዉንን ዉይይት የድምፅ ማድመፃ ማዕቀፉን በመጫን እንዲከታተሉ እንጋብዛለን።

አዜብ ታደሰ