1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ዉሎ አዳር ከጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬ ጋር

ሐሙስ፣ ጥር 18 2015

ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬ ኢትዮጵያን ከደቡብ እስከ ሰሜን ከምዕራብ እስከ ምስራቅ ተጉዛ፤ የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦችን ጎብኝታ፤ ባህላቸዉን ተዋዉቃ ኑሮአቸዉን ኖራ በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ለህዝብ «ዉሎ አዳር» በሚል ፕሮግራምዋ ከባልደረቦችዋ ጋር አቀናብራ ለሃገር የምታሳየዉ የአገርህን እወቅ ዝግጅቷ ታዋቂነትንና ተወዳጅነትን አትርፋለች።

https://p.dw.com/p/4MlKT
Äthiopien Journalistin Askale Tesefaye
ምስል privat

ዉሎ አዳር ከጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬ ጋር

ዉሎ አዳር በሚል ቅፅል ስሟ የምትታወቀዉ ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬ ኢትዮጵያን ከደቡብ እስከ ሰሜን ከምዕራብ እስከ ምስራቅ ተጉዛ፤ የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦችን ጎብኝታ፤ ባህላቸዉን ተዋዉቃ ኑሮአቸዉን ኖራ በኢትዮጵያ ቴሌቭዥን ለህዝብ «ዉሎ አዳር» በሚል ፕሮግራምዋ ከባልደረቦችዋ ጋር አቀናብራ ለሃገር የምታሳየዉ የአገርህን እወቅ ዝግጅቷ ታዋቂነትንና ተወዳጅነትን አትርፋለች። ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬ ከተጓዘችባቸዉ የኢትዮጵያ በርካታ አካባቢዎች ዉቡን ባህል ከምንጩ፤  ከህብረተሰቡ ጓዳ ቀድታ እና አብራ ኖራ፤ በበዘጋቢ ፊልም መልክ በኢትዮጵያ በቴሌቭዝን ታቅርበዉ እንጂ ዝግጅቱ ለእይታ እስኪበቃ የምትሄድበት መንገድ የምትሰራዉ ሥራ ቀላል ባለመሆኑ እጅግ ከባድና ፈታኝ ሁኔታዎችን በጥበብ አልፋ ጥዑም ዝግጅትን ማቅረቧን ያስመሰከረች ጠንካራ ጋዜጠኛ ሲሉ ብዙዎች ይመሰክሩላታል። አስካለ ተስፋዬ በዶቼ ቬለ የባህል መድረክ እንግዳ ሆና ቀርባለች።

Äthiopien Journalistin Askale Tesefaye
(ዉሎ አዳር) ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬምስል privat
Äthiopien Journalistin Askale Tesefaye
(ዉሎ አዳር) ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬምስል privat

አስካለ ተስፋዬ ወደ ጋዜጠኝነት ሞያ የገባቸዉ ከዛሬ 25 ወይም 26 ዓመት በፊት በሬድዮ የህጻናት ፕሮግራም አዘጋጅ ሆና ነዉ። የጋዜጠኝነት ሞያን ከጀመረች ሃያ አምስት አያ ስድስት ዓመት እንደሆናት የምታናገረዉ አስካለ በቴሌቭዝን ዉሎ አዳር  ዝግጅቷን ከጀመረች ግን አንድ አራት ዓመት ገደማ እንደሆናት ትናገራለች። ዝግጅቱ አስደሳች፤ ስራዉ አድካሚ ፈታኝ ቢሆንም፤ በህዝብ ዘንድ ከፍተኛ ክብርና ፍቅር አግኝቼበታለሁ ስትልም ለስራዉ ያላትን ፍቅር አፅኖት ትሰጣለች። ህዝብ ለስዋ ፍቅርና ክብር እንዳለዉ ያወቀችዉ ግን ከአንድ ዓመት ገደማ በፊት ታማ አልጋ ላይ በዋለችበት አጋጣሚ መሆኑን አትደብቅም። በኢትዮጵያ የተለያዩ አካባቢዎች ተጉዛ የብሔር ብሔረሰቦችን ባህል እና አኗኗርን አይታ እና ኖራ መልሳ ለህዝብ ለማስተዋወቅ ስትጓዝ በኖረችባቸዉ ማኅበረሰቦች ዘንድ ሁሉ ንፁህ ፍቅርን አግኝታለች፤ አብራ ማዕድ ተቀምጣ፤ ቁርበት ላይ አድራ፤ ስራዋን ጨርሳ ደህና ሁኑ ብላ ስትወጣ ከማህረሰቡ ጋር ተላቅሳ እንደምትለያየም ነግራናለች።    

Äthiopien Journalistin Askale Tesefaye
(ዉሎ አዳር) ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬምስል privat

ሰዉ ምን ያህል ገንዘብ ቢከፍል ሊያገኘዉ እና ሊያየዉ የማይችለዉን የተለያየ ማኅበረሰብ ባህል እና የአኗኗር ዘይቤ ከዝያም ደግሞ የህዝብ ፍቅር ታክሎበት በዉሎ አዳር ስራዬ አግንቻለሁ ስትል፤ አንደበተ ርትዑዋ ጋዜጠኛ ወደ ኮንሶ ተጉዛ ከማህበረሰቡ ጋር ኖራ ያየችዉን አጫወታናለች። አስካለ አብራቸዉ የኖረቻቸዉን የኮንሶ አባላት ስማቸዉን አብራቸዉ ያሳለፈችዉን ነገር ሁሉ የተረከችልን በደስታ ነዉ።   

Äthiopien Journalistin Askale Tesefaye
(ዉሎ አዳር) ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬምስል privat

ጋዜጠኛ አስካለ ስላየችዉ ነገር ስትገልፅ አንጠልጣይ በሆነ ቅላጼ ነዉ። ትረካዋን ትጀምራለች፤ ምን እንደበላች፤ ከማህበረሰቡ ጋር ምን ስትሰራ እንደዋለች፤ ምን አስደናቂ ነገር እንዳየች ትተርካለች፤ ከዝያ ደግሞ ቆም ትልና ድንቅ የሆነ ባህል፤ ገራሚ የሆነ ገጠመኝ ትላለች። ንፁህ የሆነ ፍቅር የሚገኘዉ እኮ ከከተማ ወጣ ሲባል ነዉ ስትል ፤ ደሞ ወደሌላኛዉ ገጠመኞችዋ ትረካዋን ትቀጥላለች።      

Äthiopien Journalistin Askale Tesefaye
(ዉሎ አዳር) ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬምስል privat

በደቡብ ክልል ጎፋ ዞን ማህበረሰብ ዉስጥ የሚገኙ የወጣቶች ባህላዊ የፍቅር መገላለጫ ሌላዉ ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬን የገጠማት አስገራሚ ሁኔታ ነዉ። በበሰለ እና በጥሪ ሎሚ የሚገለጽ ፍቅር። ጋዜጠኛዋ መጓዝ ወደ ፈለገቻቸዉ ቦታዎች ሁሉ ለመጓዝ ስታቅድ የአካባቢዉ የባህል  እና ቱሪዝም ቢሮ ሁሉ ተባባሪዎችዋ እንደሆኑ እና በእነሱ በኩል፤ ሁሉ ነገር ለእስዋና ለፊልም ቀራጩ ባልደረባዋ እንደሚመቻችም ነግራናለች።

Äthiopien Journalistin Askale Tesefaye
ምስል privat

ጋዜጠኛ አስካለ በትረካ ዳግም ወደ ደቡብ ክልል አባያ አካባቢ ወደ ሚኖሩ ወደ ጌዲቾ ማህበረሰብ ዘንድ ይዛንም ተጉዛለች። አስካለ ተስፋዬን በዚህ አገርህን አስተዋዉቅ የዉሉ አዳር ጉዞዋ እስካሁን የሚያስደነግጥ ወይም የሚያስፈራ ነገር አልገጠማት ይሆን? ጠይቀናታል አስካለ ከሃመሮች ጋር ዉሎ አዳር ላይ ሳለች እባብ ገጥሟታል። እንዴት አልፋዉ ይሆን? ጋዜጠኛ አስካለን ወደ ተለያዩ የኢትዮጵያ አካባቢዎች ስትጓዝ የወቅቱ የሃገሪቱ የፀጥታ ሁኔታ አያስፈራትም? ሌላዉ ያቀረብንላት ጥያቄ ነበር። አስካለ እኔ አልፈራም፤ ከከተማ ወጣ ሲባል ሁሉ ነገር ንፁህ፤  ፀጥ ያለ እና ደግነት ብቻ ነዉ ባይ ናት። ከአስካለ ጋር ያደረግነዉን ቃለምልልስ የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ!

Äthiopien Journalistin Askale Tesefaye
(ዉሎ አዳር) ጋዜጠኛ አስካለ ተስፋዬምስል privat

አዜብ ታደሰ

ታምራት ዲንሳ