1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

ከስደት የተመለሱ ዜጎችን የማቋቋም ፈተና  

ማክሰኞ፣ ጥር 28 2011

ባለፉት ሁለት ቀናት በራሳቸዉ ፈቃድ ከ300 በላይ ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች ከየመን መመለሳቸዉን ዓለም ዓቀፉ የስደተኞች ድርጅት «IOM» ገለፀ።ከስደት ወደ ኢትዮጵያዉያ የተመለሱ ዜጎችን የማቋቋም ፈተና ስደተኞችን የመመለሱ ሁኔታ ተጠናክሮ ቢቀጥልም እነሱን መልሶ በማቋቋም ረገድ ግን ችግር እያጋጠመ መሆኑም ተመልክቷል።

https://p.dw.com/p/3CXCy
Jemen Migranten
ምስል AFP/IOM

ባለፉት ሁለት ቀናት በራሳቸዉ ፈቃድ ከ300 በላይ ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች ከየመን መመለሳቸዉን ዓለም ዓቀፉ የስደተኞች ድርጅት IOM ገለፀ።ስደተኞቹ ወደሀገራቸዉ የተመለሱት ድርጅቱ ከኢትዮጵያ የዉጭ ጉዳይ ሚንስቴር ጋር ባደረገዉ ትብብር መሆኑን ድርጅቱ ገልጿል። ከስደት ወደ ኢትዮጵያዉያ የተመለሱ ዜጎችን የማቋቋም ፈተና ስደተኞችን የመመለሱ ሁኔታ ተጠናክሮ ቢቀጥልም እነሱን መልሶ በማቋቋም ረገድ ግን ችግር እያጋጠመ መሆኑም ተመልክቷል።

Äthiopien äthiopische Flüchtlinge Rückkehrer im Addis Ababa IOM Transit Center
ምስል IOM Ethiopia

የዓለም ዓቀፉ የስደተኞች ድርጅት በኢትዮጵያ የህዝብ ግንኙነት ሃለፊ አቶ ዓለማየሁ ሰይፈስላሴ ለDW እንደገለፁት ባለፉት ሁለት ቀናት ብቻ በራሳቸዉ ፈቃድ 322 ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች ከየመን ወደ ሀገራቸዉ ተመለስዋል።ስደተኞቹ በሰንዓና አካባቢዉ ለበርካታ አመታት በስደት የቆዩ ሲሆን በሀገሪቱ በተከሰተዉ ቀዉስ ሳቢያ ለከፍተኛ ችግር ተጋልጠዉ የነበሩ መሆናቸዉን ተናግረዋል። በየመን ያለዉ ቀዉስ እየጨመረ በመምጣቱም ህይወታቸዉ ለአደጋ የተጋለጡ ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች ቁጥር እየጨመረ የመጣ ሲሆን ባለፈዉ ዓመት ብቻም 156 ኢትዮጵያዉያን መሞታቸዉን ሃላፊዉ ገልፀዋል። 
እንደ ዓለም ዓቀፉ የስደተኞች ድርጅት በጎርጎሮሳዉያኑ 2018 ዓ/ም ብቻ በአካባቢዉ ከሚገኙ የአፍሪቃ ቀንድ ሀገራት  ወደ 150 ሺህ ስደተኞች ወደ ሳዉዲ ዓረቢያ ለመሻገር የመን የገቡ ሱሆን ወደ መቶ ሺህ የሚሆኑት ተሰዳጆች ኢትዮጵያዉያን ናቸዉ።ከነዚህም ዉስጥ በድርጅቱ አማካኝነት 8 ሺህ ኢትዮጵያዉያን በዚሁ ዓመት ወደ ሀገራቸዉ ተመልሰዋል።በሌላ በኩልም  ከ200ሺህ  ሺህ በላይ እትዮጵያዉያን ስደተኞችም ባለፈዉ ዓመት ከሳዉዲ አረቢያ መመለሳቸዉን የድርጅቱ የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ አብራርተዋል።በአሁኑ ወቅትም ጅቡቲ በሚገኜዉ የስደተኞች ማቆያ ጣቢያ 500 የሚሆኑ ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች ወደ ሀገራቸዉ ለመመለስ በመጠባባቅ ላይ መሆናቸዉን ድርጅቱ አመልክቷል።
ኢትዮጵያዉያን ስደተኞች ከሚገኙባቸዉ ሀገራት መንግስታትና ከዓለም ዓቀፉ የስደተኞች ድርጅት ጋር በመተባበር ለየተለያዮ ችግር የጋጠማቸዉን ዜጎች በሰላም ወደሀገራቸዉ እንዲመለሱ የማድረጉን ስራ አጠናክሮ እንደሚቀጥል የዉጭ ጉዳይ ሚንስቴር አስታዉቋል።ያም ሆኖ ግን ኢትዮጵያዉያኑ ወደ ሀገር ከተመለሱ በኋላ መልሶ በማቋቋሙ ረገድ ፈተና እያጋጠመ መሆኑን አቶ አለማየሁ አስረድተዋል። ቁጥራቸዉ እየጨመረ የመጣዉን የስደት ተመላሾች መልሶ ለማቋቋም ሙከራ ቢደረግም ከዓቅም አኳያ የሚፈለገዉን ያህል እንዳልሆነ ነዉ ያመለከቱት ። በዚህ የተነሳ ተስፋ ቆርጠዉ ድጋሜ ወደ ስደት የሄዱ መኖራቸዉን ገልፀዋል። አንዳንዶቹም በተሳሳተ ግንዛቤ ከፍተኛ ገንዘብ ከፍለዉ የተሰደዱ መኖራቸዉን ጠቁመዋል።
ስለሆነም ችግሩን ለመፍታት በሀገሬ ሰርቼ እለወጣለሁ የሚል እምነት እንዲኖር የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራ መስራትና ናየሀገር ዉስጥ የስራ ዕድል ፈጠራ ትኩረት ተጥቶ ሊሰራበት እንደሚገባ ነዉ ያሳሰቡት።ጉዳዩን በተመለከተ የኢትዮጵያ የስደት ተመላሾች ማቋቋሚያ ቢሮን ለማነጋገር ያደረግነዉ ጥረት አልተሳካም።

Jemen -  Geflohene Kinder
ምስል picture-alliance/dpa/M. Mohammed/XinHua

ፀሀይ ጫኔ

አዜብ ታደሰ 

ቀጣዩን ክፍል ዝለለዉ ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ

ተጨማሪ መረጃ ይፈልጉ