ከሞያሌ የተሰደዱ ነዋሪዎች እየተመለሱ ነዉ
ማክሰኞ፣ ሚያዝያ 2 2010በኦሮሚያ ክልል በቦራና ዞን በሞያል ከተማ የኢትዮጵያ የመከላክያ ሰራዊት በንፁሃን ዜጎች ላይ የግድያ ርምጃ መዉሰዱን ተከትሎ ወደ 50ሺህ የሚጠጉ ቀየያቸዉን ጥለዉ መፈናቀላቸዉን መዘገባችን ይታወሳል።ወደ ጎረቤት አገር ኬንያ ተሰደዉ በካምፕ ዉስጥ የሚገኙት ወደ 10, 500 እንደሚጠጉም የኬንያ ቀይ-መስቀል ማኅበር መረጃ ያመለክታል።
በመጋቢት ወር 2010 ዓ,ም የመጀመርያ አካባቢ የስደተኞቹ ቁጥር እንደሚጨምር የኬንያ ቀይ-መስቀል ማኅበር የሕዝብ ግኑኝነትና የኮሙኒኬሽን አስተዳዳር ኖኤላ ናሙላንዳ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዉ ነበር። ይሁን እንጂ እስካሁን ቁጥራቸዉ ጭማሪ እንዳላሳየና የሰብዓዊ ሁኔታዉ መቆጣጠር እንደተቻለ የማኅበሩ የአከባቢዉ የቀይ መስቀል ዋና ስራ አስከያጅ ታላሶ ቹቻ ዛሬ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል።
ታላሶ ቹቻ: «የሰብዓዊ ሁኔታዉ አስቸኳይ ከነበረበት ደረጃ አሁን ዝቅ ብለዋል። ምክንያቱም የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነርን ጨምሮ ሌሎች በስደተኞች ዙርያ የሚሰሩ ድርጅቶች በመሳተፋቸዉ ነዉ። አሁን ሁለት የስደተኞች መጠለያ ነዉ ያለዉ። አንዱ በኬንያ ሞያሌ የሚገኘዉ የሶማሬ ካምፕ ሲሆን በዚህ መጠለያም 777 ግለሰቦች ተጠልለዉ ይገኛሉ። ሁለተኛዉ በሶሎሎ ዉስጥ የሚገኘዉ የዳምባላ ፋቻና መጠልያ ሲሆን በዚህ መጠለያም 1,819 ግለሰቦች ይገኛሉ። እነዚህ ግለሰቦች በመጠለያዉ የተመዘገቡ ስሆኑ ቀሪዎቹ ወደ 5000 የሚሆኑት ደግሞ ምዝገባን እየተጠባበቁ ይገኛሉ።»
ባላፈዉ ሳምንት ሰኞ አዲሱ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚንስትር የክተር አብይ አህመድ መሾምን ተከትሎ ብዙ ሰዎች ወደ አገራቸዉ እንደተመለሱም ዋና ስራ አስካያጇ ታላሶ ለዶይቼ ቬሌ ተናግረዋል። ታላሶ ቹቻ: «ጠቅላይ ሚንስትሩ የመሾማቸዉ መግለጫን ተከትሎ ወደ መጠለያ የሚመጡት ስደተኞች ቁጥር በጣም ቀንሰዋል። ከባለፈዉ ሳምንት ጀምሮ 11 አባወራዎችን ብቻ ነዉ የተቀበልነዉ። ቁጥራቸዉ ከቀን ወደ ቀን እየቀነሰ ይገኛል። በአከባብያቸዉ ሁኔታዉ ቀስ በቀስ ወደ ነበረበት እየተመለሰ ነዉ።»
ወደ ኬንያ ገቡ ከተባሉት 10, 500 ተፈናቃዮች ዉስጥ 80 በመቶ የሚሆኑት ሴቶችና ሕጻናት መሆናቸዉን የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ጉዳይ ከፍተኛ ኮሚሽን ባወጣዉ ዘገባ አስታውቋል። ወደ 1500ዎቹ ከአምስት ዓመት እድሜ በታች መሆናቸው እና 600 ነፍሰ ጡር እናቶች እንደሆኑ ተገልጿል። የአካል ጉዳተኞች እና አረጋውያን ከተሰደዱት መካከል ይገኙበታል።
መርጋ ዮናስ
ሂሩት መለሰ