ከሕግ አግባብ ውጪ በእስር ላይ የሚገኙ ሰዎች እንዲለቀቁ ኢሰመኮ ጠየቀ
ሐሙስ፣ ግንቦት 11 2014ማስታወቂያ
ከሕግ ውጪ በእስር ላይ የሚገኙ የኦሮሞ ነፃነት ግንባር (ኦነግ) አባላት በአፋጣኝ ከእስር ሊለቀቁ ይገባል ሲል የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ጠየቀ።
ኮሚሽኑ ሌሎች ከዚህ ቀደም ክስ ሳይመሰረትባቸው የታሰሩ ሰዎች በአፋጣኝ ከእስር ሊለቀቁ ይገባል ብሏል። ኢሰመኮ አደረግሁት ባለው ምርመራ ፍርድ ቤት በዋስትና እንዲለቀቁ የፈቀደላቸው፣ ምንም አይነት ክስ ያልተመሰረተባቸው ፣ ከወራት እስከ 2 ዓመት ለሚሆን ጊዜ በተለያዩ ቦታዎች እየተዘዋወሩ ከሕግ ውጪ በእስር ላይ እንደሚገኙ ገልጿል። በእስሩ ሂደት ተገቢ ባልሆነ አያያዝ እና ድብደባ ለተለያዩ የአካል ጉዳቶችና የጤና እክል የተጋለጡም መኖራቸውን ማረጋገጡን አስታውቋል።
ኮሚሽኑ ሰዎችን ክስ ሳይመሰረትባቸው ለረዥም ጊዜ ማሰር ዜጎች በፍትሕ አስተዳደር ላይ ያላቸውን እምነት ያሳጣል በማለትም ታሳሪዎች በሕጋዊ ሂደት እንዲዳኙ ጠይቋል።
ሰለሞን ሙጬ
ልደት አበበ
ኂሩት መለሠ