ኢትዮጵያዊው ሹራ ቅጣታ የለንደን ማራቶን የሩጫ ውድድርን አሸነፈ
እሑድ፣ መስከረም 24 2013ማስታወቂያ
ኢትዮጵያዊው ሹራ ቅጣታ የለንደን ማራቶን የሩጫ ውድድርን አሸነፈ። ኬንያዊው ኢሉድ ኪፕቾጌ ስምንተኛ ሆኖ ውድድሩን አጠናቋል። ሹራ ውድድሩን በ2 ሰዓት ከ5 ደቂቃ ከ41 ሰከንድ በማጠናቀቅ ያልተጠበቀ አሸናፊ ሆኗል።
ኬንያዊው ቪንሰንት ኪፕቹምባ ሁለተኛ ኢትዮጵያዊው ሲሳይ ለማ ሶስተኛ ሆነው ውድድሩን አጠናቀዋል። ሶስተኛ የወጣው ሲሳይ ውድድሩን ለመጨረስ 2 ሰዓት ከ5 ደቂቃ ከ45 ሰከንድ ፈጅቶበታል።
የዓለም የማራቶን ክብረ ወሰን ባለቤት የሆነው ኬንያዊው ኢሉድ ኪፕቾጌ በውድድሩ መገባደጃ ወደ ኋላ ቀርቶ ከአሸናፊው አንድ ደቂቃ ከአንድ ሰከንድ በመዘግየት አጠናቋል።
የወንዶቹ ውድድር በኢትዮጵያዊው ቀነኒሳ በቀለ እና ኬንያዊው ኢሉድ ኪፕቾጌ መካከል ብርቱ ፉክክር ይደረግበታል ተብሎ ይጠበቅ ነበር። ይሁንና በልልምድ ወቅት ጉዳት የገጠመው ቀነኒሳ ባለፈው አርብ ከውድድሩ ራሱን በማግለሉ በጉጉት ይጠበቅ የነበረው ፉክክር ሳይሳካ ቀርቷል።
በሴቶች ኬንያዊቷ ብሪጅድ ኮስጌይ ውድድሩን በበላይነት አጠናቃለች። ብርጂድ ውድድሩን ለማጠናቀቅ 2 ሰዓት ከ18 ደቂቃ ከ58 ሰከንድ ፈጅቶባታል። አሜሪካዊቷ ሳራ ሖል ሁለተኛ፣ ኬንያዊቷ ሩዝ ቼፕንጌች ሶስተኛ በመሆን ውድድሩን ጨርሰዋል።
እሸቴ በቀለ