ትምህርት እና ስራ በረመዳን ፆም ወቅት
ዓርብ፣ ግንቦት 9 2011የኢትዮጵያ ትምህርት ሚኒስቴር ከህብረተሰቡ በቀረበለት ጥያቄ መሰረት የዘንድሮ ሀገር አቀፍ የ8ኛ 10ኛ እና 12ኛ ክፍል ፈተናዎች መስጫ ቀናት ከታቀዱበት ቀናት መቀየራቸውን አስታውቋል። ይህም ከኢድ አልፈጥር በዓል ጋር በተያያዘ «አመቺ ሁኔታ ለመፍጠርና የፈተናውን ሂደት የተሳካ ለማድረግ» መሆኑን ሚኒስቴሩ ገልጿል።ምንም እንኳን የጀርመን ትምህርት ቤቶች መልቀቂያ ፈተናውን ለመስጠት በመንግሥት ደረጃ ባይገደዱም አንዳንድ ትምህርት ቤቶች ግን ከጾሙ ጋር በተያያዘ ከማትሪክ ፈተና በኋላ ይካሄዱ የነበሩ ድግሶችን ለሙስሊም ተማሪዎች ሲሉ መቀየራቸውን እየገለፁ ነው። ከዚያ በላይ አነጋጋሪው ግን ለረዥም ሰዓታት ምግብ ሳይበሉ እና ሳይጠጡ የሚቆዩት የመለስተኛ እና ሁለተኛ ደረጃ ተማሪዎች ጤንነት ነው። አቅም አጥቶ የሚወድቅን ተማሪ መምህር ውኃ እንዲጠጣ ማስገደድ ይችላል? ወይስ በኃይማኖት ነፃነት ጣልቃ መግባት ነው? ይህ በጀርመን ሲሆን ኢትዮጵያ ውስጥ የ8ኛ ክፍል ተማሪ የሆነው ሁሴን ትምህርት ቤት ውስጥ ጿሚ ተማሪዎች ላይ የታዘበውን ገልፆልናል። « ትንሽ የመድከም እና የመሰልቸት ባህሪ ይታያል። መምህራንም ለማበረታታት ይሞክራሉ። ማታ ማታ የምትቀመጡ ከሆነ እያነበባችሁ እንጂ እየቃማችሁ አይሁን ይላሉ።»ሁሴን እንደሚለው ተማሪዎቹ በማንም አካል ጫና ሳይደረግባቸው በራሳቸው ፍላጎት ነው የሚፆሙት።
በጀርመን ሀምቡርግ ከተማ በሚገኝ አንድ ኔልሰን ማንዴላ በተባለ ትምህርት ቤት መምህርት የሆኑት አስትሪድ ሳንደርስ ለጀርመን ዴር ሽፒግል ጋዜጣ እንደገለፁት በትምህርት ቤቱ 85 በመቶ ያህሉ ተማሪዎች የእስልምና ዕምነት ተከታዮች ናቸው። አብዛኞቹም በረመዳን ወር ይፆማሉ። መምህርቷ እንደሚሉት ተማሪዎቹ በቤተሰብ ጫና አይደለም የሚፆሙት። ይልቁንም ፈልገው ነው። ነገር ግን ማን ረዥም ሰዓት ይፆማል የሚል ፉክክር በተማሪዎቹ ዘንድ ማስተዋላቸውን ያስረዳሉ። በጀርመን ሀገር ፆሙን አድካሚ የሚያደርገው ረመዳን በበጋ ወር ሲውል ሙስሊሞች እስከ ምሽቱ አራት እና አምስት ሰዓት ለመፆም ስለሚያስገደዱ ነው።
ወደ ኢትዮጵያ ስንመለስ ጣሲም የ 12ኛ ክፍል ተማሪ ነው። በቅርቡ ወሳኝ ፈተና ይጠብቀዋል። ጥናቱ እና ፆሙ ብዙም አብሮ አይሄድም ይላል።ይሁንና ፆሙን ለማቋረጥ የሚያስገድደው ደረጃ ላይ አይደለም ። በዛ ላይ ጣሲም የ10ኛ ክፍል መልቀቂያ ፈተና ሲፈተንም የፆም ወቅት ስለነበረ ልምዱ እንዳለው ይናገራል። የ17 ዓመት ወጣቷ አሚራ ግን በፍፁም አይከብድም ትላለች።
ኢትዮጵያ ውስጥ በትምህርት ላይ የሚገኙ ወጣቶች ብቻ ሳይሆኑ በስራው ዓለም የተሰማሩ እንደ እንድሪስ ያሉ ወጣቶችም ተሞክሯቸውን አካፍለውናል። እንድሪስ በግብርና ስራ ነው የተሰማራው« ፀሀይ እንዳይመታኝ ፀሀይ በማይበዛበት ሰዓት እሰራለሁ። ሐይማኖታችንም ስራ ፍቱ አይልም። ላለመለመን ላለመቸገር እንሰራለን።» ሌላው ሠራተኛ ደግሞ በንግድ ስራ ላይ ተሰማራው ሰኢድ ነው። « ፆሙ ከሌሎቹ ጎዜያት የዘንድሮው ደስ ይላል።»
ተሰሚነት ካገኘው የሙስሊሞች ጉዳዮች አንዱ ባለፈው ሳምንት በትምህርት ሚኒስቴር በኩል እንዲቀየሩ የተደረገው የዘንድሮው ሀገር አቀፋዊ ፈተናዎች መስጫ ቀናት ናቸው። እንዲቀየር ጥያቄ ካቀረቡት አንዱ የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ ሰብሳቢ ኡዝታዝ አቡበክር አህመድ ሙሃመድ ናቸው።« የሚመለከተው አካል የተደረገው ነገር ስህተት እንደሆነ አምኖ አስተካክሏል። ይህ በመደረጉ እናመሰግናለን።»
የረመዳንን ፆም መፆም ያለበት ማነው? ኡዝታዝ አቡበክር አህመድ የሰጡንን ማብራሪያ ከዚህ በታች በድምፅ መከታተል ይችላሉ።
ልደት አበበ
ሂሩት መለሰ