ታስረዉ የነበሩ 1174 የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ተለቀቁ
ዓርብ፣ ጥቅምት 9 2011
በጦላይ ተይዘዉ የቆዬት የአዲስ አበባ ነዋሪዎች በሕገ-መንግስት፣ በሕግ የበላይነት እንዲሁም ወጣቶች በሀገር ግንባታ ያላቸው ሚና ላይ ስልጠና ሲወስዱ እንደነበር ተመልክቶአል። ወጣቶቹ «ለሕንጸት» ሲባል ወደ ጦላይ ተልከዋል ከተባለ በኃላ ሥለ እስረኞቹ ወሬ ባለመነሳቱ ኢትዮጵያዉያን «በግፍ የተያዙ የአዲስ አበባ ወጣቶች ይፈቱ» የሚል ትናንት የተጠናቀቀ የሦስት ቀናት ዘመቻ በማኅበራዊ መገናኛ ዘዴዎች ማካሄዳቸዉ ይታወሳል። በዘመቻዉ «በግፍ የተያዙ የአዲስ አበባ ወጣቶች ይፈቱ»፤ «ጫት መቃምና፤ ሃሺሽ ማጤስ፤ በሕግ አልተከለከለም»፤ «ፍትህ በገፍ ለታሰሩት አዲስ አበቤዎች» የሚሉ ጽሑፎችን በብዛት ተራጭተዉ ነበር። የኢትዮጵያ መንግሥት አዲስ አበበባ ዉስጥ በሺ የሚቆጠሩ ሰዎችን በጅምላ ማሰሩን ተከትሎ ዓለም አቀፉ የመብት ተሟጋች ድርጅት አምንስቲ ኢንተርናሽናል «መንግሥት ሕግ ለማስከበር ሕገ-ወጥ መሆን የለበትም» ሲል የመንግሥትን ርምጃ በማዉገዝ መግለቻ ማዉጣቱም ይታወሳል። ዘመቻዉን ተከትሎ የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ኮሚሽነር ዘይኑ ጀማል ለ«DW» በሰጡት ቃለ ምልልስ የተያዙት ወጣቶች ብቻ አይደሉም፤ ታሳሪዎችም አይባሉም፤ የሎጂስቲክ ችግር እስካላጋጠመን እስከ ፊታችን ሃሙስ ጥቅምት «8» ድረስ ይለቀቃሉ ብለዉ ተናግረዉ ነበር። ከጦላይ ዛሬ የወጡትን የአዲስ አበባ ነዋሪዎች ጉዳይ በተመለከተ የአዲስ አበባዉ ወኪላችን ዝርዝር ዘገባ ልኮልናል።
ጌታቸዉ ተድላ ኃይለጊዮርጊስ
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ