ባላደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ ዛሬ ከባሕር ዳር ከተማ ነዋሪዎች ጋር ውይይት አደረገ
ቅዳሜ፣ የካቲት 7 2012የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች በዋናነት ወጣቶች በጠዋት ነበር የባላራሱን ሊቀመንበር እስክንድር ነጋን ለመቀበል በባሕር ዳሩ አፄ ቴዎድሮስ ስታዲዮም የተገኙት፡፡ በስታዲዮሙ አዲስ አበባን የሚወድሱ ሙዚቃዎች ከፍ ባለ ድምፅ ሲሰሙ ነበር፡፡የባላደራስ ለእውነተኛ ዴሞክራሲ ፓርቲ ሊቀመንበር አቶ እስክንድር ነጋ ወደ ስታዲዮሙ ሲገቡ ሞቅ ያለ አቀባበል ነው ከታዳሚው የተቸራቸው፡፡አቶ እስክንድር ከባህር ዳር ህዝብ ጋር ለመወያየት ባለፈው ሰኔ 15/2011 ዓም ወደ ባሕር ዳር መጥተው የነበረ ቢሆንም በእለቱ በክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ላይ በተፈፀመ ግድያና በተፈጠረው አለመረጋጋት ምክንያት የመጣበትን ዓላማ ሳያሳኩ እንደተመለሱ በመድረኩ ተናግረዋል፡፡
አቶ እክንድር ዛሬ ለተከታዮቻቸው እና ለደጋፊዎቻቸው ባደረጉት ንግግር በመጪው ምርጫ ፓርቲያቸው በፌደራል ተወካዮች ምክርቤት የአዲስ አበባ ከተማን የውክልና መቀመጫ በሙሉ እንደሚያሸንፉ በእርግጠኝነት ተናግረዋል፡፡
ምርጫን ለማሸነፍና የተለያዩ ወንጀል የሰሩ አካላትን በህግ ለመጠየቅ ሁሉም በምርጫ በመሳተፍ እውነተኛ የህዝብ ልጆችን ሊመርጥ አንደሚገባም ተናግረዋል፡፡
በአዲስ አበባ በቅርቡ የተፈፀሙ ግድያዎችን በእጅጉ አንደሚያወግዙ የተናገሩት አቶ እስክንድር ይህን ታሪክ ለመቀየር በትጋት እንደሚሰሩ አመልክተዋል፡፡ የደምቢዶሎ ዩኒቨረሲቲ ተማሪዎችን ያገቱ ወገኖች ተማሪዎን እንዲለቁ የተማፅዕኖ ጥሪም አስተላልፈዋል፡፡
ዓለምነው መኮንን
ታምራት ዲንሳ
ልደት አበበ