1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በፀጥታ ኃይሎች ጥብቅ ቁጥጥር በውስን ሰዎች የተከበረው ኢሬቻ ሆራ አርሰዲ

እሑድ፣ መስከረም 24 2013

"ኢሬቻ ሰው የሚመጣው ሰላም ለመለመን ነው፤ ዝናብ ለመለመን ነው። ኢሬቻ ኦሮሞ ከተለያየ አካባቢ የሚመጣበት ነው። አንድነቱን የሚያከብርበት ጊዜ ነው" ያለ አንድ የበዓሉ ተሳታፊ "ይኼን ህዝብ ግማሹን ቅር ብለህ ግማሹን ና ማለት በጣም ይከብዳል" ሲል የተሳታፊዎች ብዛት መገደብ የፈጠረበትን ቅሬታ ለዶይቼ ቬለ ተናግሯል።

https://p.dw.com/p/3jPhn
Äthiopien | Oromo Thanksgiving Irreecha in Bishoftu
ምስል Seyoum Getu/DW

ኢሬቻ ሆራ አርሰዲ በቢሾፍቱ ተከበረ

 

ከፍተኛ የፀጥታ አካላቱ ፍተሻ እና ዝውውር ከትናንት ጀምሮ ነግሶባት የቆየው የቢሾፍቱ ከተማ ዛሬ እሬቻ ሆራ አርሰዲን አክብራ ዋለች፡፡ የቢሾፍቱ እሬቻ ሆራ አርሰዲ በቁጥር እጅግ ውስን ሰዎች ብቻ በተገኙበት ነው ተከብሮ የዋለው፡

ወትሮም ከተማዋ ልትሸከመው ከምትችለው በላይ እንግዶችን ለእሬቻ ሆራ አርሰዲ ከአራቱም አቅጣጫዎች ተቀብላ ስታስተናግድ ለኖረች ቢሾፍቱ ይህ ከተለመደው አንጻር ቁጥሩ እጅጉን ያነሰ ከመሆኑ ባለፈም፤ ያዘን ያህል የተቀዛቀዘ ነው፡፡

Äthiopien | Oromo Thanksgiving Irreecha in Bishoftu
በፀጥታ ኃይሎች ጥብቅ ቁጥጥር በውስን ሰዎች የተከበረው ኢሬቻ ሆራ አርሰዲምስል Seyoum Getu/DW

ከቅዳሜ ጀምሮ ወደ ቢሾፍቱ ከተማ መግባት የሚፈቀድለት ሰው የይለፍ ካርድ የያዘ አለዚያም የከተማዋ የነዋሪነት መታወቂያን የያዘ ብቻ ነው፡፡ በየአቅጣጫው ከተማዋን የከበቡ የመንግስት የጸጥታ ኃይሎች የመግቢያ ካርድ እና የከተማዋ የነዋሪነት መታወቂያ ከያዙት ውጪ ወደ ከተማዋ መግባት የሚሻን ማንኛውንም ሰው ወደ መጡበት እንዲመለሱ ያስገድዱ ነበር፡፡

ከለሊቱ ዘጠኝ ሰዓት ጀምሮ ወደ ሆራ አርሰዲ ሃይቅ የሚደረግ ጉዞ ሲጀምርም ሲደረግ የነበረው ፍተሸና ብርበራ ከፍተኛ የሚባል ነው፡፡ ወደ ስፍራው ሲጓዙ የነበሩ አምቦላንሶችና የአደጋ ጊዜ ሰራተኞች፣ የመገናኛ ብዙሃን ሙያተኞች አንኳ ሳይቀሩ ከፍተኛ ቁጥጥርና ፍተሻ ሲደረግባቸው ነበር፡፡ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የሀገር መከላከያ እና የኦሮሚያ ልዩ ሃይሎች በከተማዋ ወዲያ ወዲህ ስዘዋወሩም ይታያሉ፡፡

ወትሮም በሚሊዮኖች የሚጨናነቀው የሆራ አርሰዲ ሃይቅ አባገዳዎች፣ ሃዳሲንቄዎችና ወጣቶች በተገኙበት በውስን ሰዎች ብቻ ነው የተከበረው፡፡ ከለሊት እስከ ማምሻው በውስጧ በሚርመሰመሱ የበዓሉ ታዳሚ እንግዶች የምትጨናነቀው ቢሾፍቱ ዛሬ ግን የገበያን ያህል አንኳ ሳትደምቅ ነው የዋለችው፡፡ የኢሬቻ ስነስርዓቱም ቢሆን ገና በሶስት ሰዓት ገደማ ተፈጽሞ ተጠናቋል፡፡

በየቦታው ተቧድነው የተለያዩ አከባቢዎች የኦሮሞ ባህላዊ ጨዋታዎችን የሚያደምቁ ወጣቶችም ዛሬ በዚያ የሉም፡፡ መግቢያ ያልያዙ በርከት ያሉ ወጣቶችና አንግዶች ወደ እሬቻው ስፍራ ለመጓዝ ጥረት ቢያደርጉም መግቢያ ካርድ አልያዛችሁም በሚል በፀጥታ ኃይሎች ተከልክለዋል፡፡

Äthiopien | Oromo Thanksgiving Irreecha in Bishoftu
በፀጥታ ኃይሎች ጥብቅ ቁጥጥር በውስን ሰዎች የተከበረው ኢሬቻ ሆራ አርሰዲምስል Seyoum Getu/DW

በዘንድሮ የእሬቻ ክብረ በዓል ላይ ውስን ሰዎች ብቻ እንዲታደሙ ውሳኔ የወሰደው መንግስት ምክኒያቱንም የኮሮና ተዋሲ ወረርሽኝ ሲል ያስቀምጣል፡፡ ነገር ግን በዚህ ደረጃ የሰው ቁጥር አንሶ እሬቻ እንዲደረግ የተወሰነው በኮሮና ምክኒያት ብቻ አይደለም ብለው የሚያምኑ በርካቶች ናቸው፡፡ በእሬቻ የሚሳተፉ ሰዎች ቁጥረ በጥቅ ተሳታፊዎች እንዲወሰን ወቅታዊው የፖለቲካ ትኩሳቶች መንግስት ላይ ተቃውሞ እንዳያስነሳ ስጋት በመፈጠሩም ጭምር ነው ሲሉ በሆራ አርሰዲ ከታደሙት ተሳታፊዎች ለዶይቼ ቨሌ የተናገሩ አሉ።

ስዩም ጌቱ

እሸቴ በቀለ