1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በጦርነት የተጎዱ 1107 የአማራ ክልል የጤና ተቋማት ስራ ጀመሩ

ሐሙስ፣ መስከረም 26 2015

ህወሓት በአማራ ክልል በቆየባቸውጊዜያት የተጎዱ የተባሉ 1107 የጤና ተቋማት ተጠግነውና ቁሳቁሳቸው በከፊል ተሟልቶ መሰረታዊ አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነ የአማራ ክልል ጤና ቢሮ አስታወቀ። በሌላ በኩል የባህር ዳር ፈለገህይወት አጠቃላይ ስፔሻላዝድ ሆስፒታል አገልግሎት ማሻሻሉን ባለሙያዎችና ታካሚዎች ለዶቼቬለ ተናግረዋል።

https://p.dw.com/p/4Hqm6
Äthiopien | Felegehiwot Comprehensive Specialized hospital in Bahidar
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

በጦርነት የተጎዱ የአማራ ክልል የጤና ተቋማት

“ትልቅ ጉዳይ የነበረው ከጦርነቱ ጋር የነበሩት ችግሮች ናቸው፣ ጦርነቱ ብዙ ችግሮችን ነው ያደረሰው 1107 የሚደርሱ ተቋማት ናቸው የተጎዱብን…ከክልሉ አጠቃላይ ካሉ የጤና  ተቋማት 56 ከመቶ የሚሆኑ ነው የተጎዱት በዚህ ጦርነት፣ ህንፃቸው በከባድ መሳሪያ ተመትቶ ነበር፣ የህክምና መሳሪዎች የተዘረፉት ተዘርፈዋል፣ ያሉት ደግሞ እንዳሰሩ ተደርገው ውስጣቸው የሚቆረጠው ተቆርጦ ተመልሰው መጠገን በማችሉበት ደረጃ ነበር ያሉት ወደ 118 የሚሆኑ አምቡላንሶች ናቸው የተቃጠሉብን፣ የወደሙብን ብዙ ችግር የደረሰባቸው፡፡” ነው ያሉት ኃላፊው፡፡
አጠቃላይ ጉዳቱ ኮሚቴ ተዋቅሮ በእያንዳንዱ ሆስፒታል፣ ጤና ጣቢያና ጤና ኬላ ዝርዝር ጥናት መደረጉንና የጉዳቱ መጠንም በገንዘብ ከ13 ቢሊዮን ብር በላይ እንደሆነም አስረድተዋል፡፡ እንደ ኃላፊው ገለፃ በጦርነቱ በርካታ የአማራ ክልል ህዝብ ለጤና አገልግሎቶች ችግሮች ተዳርጎ ቆይቷል፡፡ተቋማቱ ከመንግስት፣ መንግስታዊ ካልሆኑ ተቋማትና ግለሰቦች በተገኘ ድጋፍ መሰረታዊ የጤና አገልግሎቶችን መስጠት የሚያስችል ደረጃ ላይ እንደሚገኙም ዶ/ር መልካሙ አብራርተዋል፡፡“እነዚህ ተቋሞች ብዙ ነገራቸው ገና አልተሟላም መስራት የሚችሉት መሰረታዊ የሆነውን የድንገተኛ አገልግሎቶችን ነው እናቶችን ማከም፣ እናቶችን ማዋለድ፣ ህፃናትን ማከም ገና አሁንም ብዙ መስራት ይጠበቅባቸዋል፣ ቀሪ የጎደሉ ነገሮችን ከአጋሮቻችን ጋር በመሆን የምናስተካክላቸው ናቸው ”
የሰሜን ወሎ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ ሲስተር ፈለቁ መኮንን ተቋማቱ አገልግሎት መስጠት መጀመራቸውን ገልጠዋል፡፡

Äthiopien | Melkamu Abte
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

ይህ በእንዲህ እንዳለ ቀደም ሲል በአገልግሎት አሰጣጡ ቅሬታ ይቀርብበት የነበረው የባህር ዳር ፈለገ ህይወት አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል አሁን የተሻለ አገልግሎት እየሰጠ እንደሆነ ታካሚዎች ተናግረዋል፡፡የሆስፒታሉ ስራ አስኪያጅ አቶ አቢይ ፍሰሐ በርካታ ማሻሻያዎች በሆስፒታሉ መደረጉን ይናገራሉ፡፡ “አንደኛው ዋና ችግር የነበረው የሰው ኃል ነው፣ በተለይ ስፔሻሊስቲና ሰብ ስፔሻሊስት አልነበረውም ከጤና ቢሮ ጋር በመሆን… 60 የሚሆኑ ተጨማሪ የህክምና የስፔሻሊስቲና ሰብ ስፔሻሊቲ ዶክተሮችን በማሟላት የጠቅላላ ሀኪሞችን ቁጥር ከ20 ወደ 140 አሳድገነዋል፣ በሽተኛ የሚተኛ ሲመጣ የሚተኛው ወለል ላይ ነበር ጭቅላ ህጻናት፣ ወላድ መጥተው መሬት ላይ ነው የሚተኙ የነበረው ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባባር ባለ 5 ወለል ህንፃ አገኘን ማንኛውም ሰው መሬት የማይተኛበትን ስርኣት ዘረጋን፡፡”የባህር ዳር ፈለገ ህይወት አጠቃላይ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል  ከ8 ስከ 10 ሚሊዮን ለሚሆኑ የአማራና አጎራባች ክልሎች አገልግሎት የሚሰጥ ሲሆን በዓመት በአማካይ እስከ 300ሺህ ህሙማንን ያስተናግዳል፣ ሆስፒታሉ 560 ቋሚ አልጋዎችና ከ1ሺህ 500 በላይ ቋሚና ጊዜያዊ ሰራተኞችም  አሉት፡፡
ዓለምነው መኮንን
ኂሩት መለሰ

Äthiopien | Akten der Krankengeschichte der Patienten
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

እሸቴ በቀለ