በኮንጎ 700 ለሚሆኑ የፖለቲካ እስረኞች ምህረት ተደረገ
ሐሙስ፣ መጋቢት 5 2011ማስታወቂያ
አዲስ ተመራጩ የኮንጎ ፕሬዚዳንት ፌልክስ ትሲኪዲ በቀድሞዉ ፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላ መንግሥት ለታሰሩ ወደ 700 የፖለቲካ እስረኞች ምህረት አደረጉ። ትናንት ከእስር ከተለቀቁት እስረኞች መካከል የሐገሪቱን የፀጥታ ሁኔታ ረብሻችኋል በሚል በካቢላ መንግሥት ታስረዉ የነበሩት ሦስቱ ታዋቂ የመንግሥት ተቃዋሚ ፖለቲከኛ ፋራንሲክ ዲኦንጎ፤ ዲዮሚ ዶንጋላ እና ፊርሚን ያንጋምቢ ይገኙበታል። ይህ የፖለቲካ እስረኞች የመልቀቅ ርምጃ የመጣዉ አዲስ ተመራጩ የኮንጎ ፕሬዚደንት ፌልክስ ትሲዲኪ ስልጣን በያዝኩ በመጀመርያዎቹ 100 የስልጣን ቀናቶች ዉስጥ የፖለቲካ እስረኞችን እፈታለሁ ሲሉ ቃል መግባታቸዉን ተከትሎ ነዉ። አዲሱ የኮንጎ ፕሬዚዳንት ፌልክስ ትሲኪዲ በጎርጎረሳዉያኑ 2018 መጨረሻ የተካሄደዉን የኮንጎ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ያሸነፉና በኮንጎ ታሪክ ሃገሪቱ ከቤልጂየም ቅኝ ግዛት ከወጣች ከ 1960 በኋላ ለመጀመርያ ጊዜ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር የተደረገበት ነዉ ተብሎአል። አዲሱ የኮንጎ ፕሬዚዳንት ፌልክስ ትሲኪዲ በሃገሪቱ ሙስናን እንደሚዋጉ እንዲሁም የሃገሪቱን የፖለቲካ ምህዳር እንደሚያሰፉ ቃል ገብተዋል።
አዜብ ታደሰ
ሸዋዬ ለገሠ