በአዲስ አበባ የሞተር ብስክሌቶች እገዳ
ረቡዕ፣ ሰኔ 12 2011የከተማው ሰላም በተረጋጋ ሁኔታ እየቀጠለ ቢሆንም በተደረገ ጥናት በህዝቡ ላይ የስነልቦና ጫና ለማሳደር ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በተደራጀ መንገድ የቅሚያ፣ የስርቆት እና አልፎ አልፎ ዝርፊያ እየተፈጸመ መሆኑ ነው የተገለጸው። ለዚህም ሰሌዳቸው አዲስ አበባ ያልሆኑ ሞተር ብስክሌቶች ዋነኛ የችግሩ ምንጭ መሆናቸውን በማመልከት ነው የከተማዋ ምክትል ከንቲባ ከተጠቀሰው ቀን ጀምሮ ሙሉ በሙሉ እንዳይንቀሳቀሱ መታገዳቸውን ያመለከቱት። ይሁንና ፖስተኞች ፣ ኤምባሲዎች እና ሌሎች የግል ተቋማት እንደገና ፍቃድ አውጥተው በጥብቅ ኃላፊነት ሊጠቀሙ እንደሚችሉም ተገልጿል። በመሆኑም ባለንብረቶች ንብረታቸውን እንዲሰበስቡ እና ከከተማው እንዲያስወጡ ነው ማሳሰቢያ የተሰጠው።
ሌላ አማራጭ ጠፍቶ ነው ይህ ውሳኔ የተላለፈው ለሚለውም ፤ ከንቲባው «ሞተር ብስክሌቶች የትራንስፖርት አማራጭ አይደሉም» ብለዋል። በሌላ በኩል የጭነት ተሽከርካሪዎች ከተማዋን እያጨናነቁ በመሆኑ ከሰኔ 30 ጀምሮ ማንኛውም የመጫንና የማውረድ አገልግሎት የሚሰጡ ተሽከርካሪዎች ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ ምሽቱ 2 ሰዓት እንዳይንቀሳቀሱ መታገዳቸውን ምክትል ከንቲባው አመልክተዋል።
በቀጣይ ግን የግዙፍ ግንባታዎች እና የመንግሥት ተቋማት በልዩነት እንደገና ተመዝግበው እንዲንቀሳቀሱ የሚደረግበት ዕድል ይኖራል ብለዋል። የ2 ቁጥር ሰሌዳ ባላቸው አነስተኛ ተሽከርካሪዎች እና በታክሲዎች በተመሳሳይ እየተፈጸመ ያለን ዝርፊያ እና ወንጀል ለመከላከል በሂደት የምንሠራበት ነው ብለዋል።
ሰሎሞን ሙጬ
ሸዋዬ ለገሠ
ተስፋለም ወልደየስ