በአማሮ ልዩ ወረዳ ታጣቂዎች 6 ሰዉ ገደሉ
ማክሰኞ፣ የካቲት 30 2013ማስታወቂያ
በደቡብ ክልል አማሮ ልዩ ወረዳ ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት ስድስት ሰዎች ተገደሉ። ሰዎቹ የተገደሉት ልዩ ወረዳውን ከኦሮሚያ ምዕራብ ጉጂ ዞን በሚዋስነውና ዳኖ በተባለ የገጠር ቀበሌ ውስጥ ነው። በጥቃቱ ከተገደሉት መካከል የልዩ ወረዳው የብልጽግና ጽሕፈት ቤት ኃላፊና አንድ የፖሊስ ባልደረባ እንደሚገኙበት የአማሮ ልዩ ወረዳ ሰላምና ጸጥታ ጽሕፈት ቤት ባለስልጣናት ገልጸዋል። ጥቃቱ የደረሰው የአማሮ እና የጉጂ ተጎራባች ነዋሪዎች በእርቅ ጉዳይ ላይ ለመምከር ከሀገር ሽማግሌዎች እና ከሁለቱ መስተዳደር አመራር ጋር በተሰበሰቡበት ወቅት ነው። ባለፉት ሦስት ዓመታት በደረሱ ተመሳሳይ ጥቃቶች ከአንድ መቶ በላይ ሰዎች መገደላቸውን ጥናቶች ያመለክታሉ። በሺህዎ የሚቆጠሩም ከቀዬያቸው ተፈናቅለዋል።
ሸዋንግዛዉ ወጋየሁ
ማንተጋፍቶት ስለሺ
አዜብ ታደሰ