1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በአማራ ክልል ም/ቤቶች አዳዲስ ድምፆች

ረቡዕ፣ ሰኔ 16 2013

በአማራ ክልል አንዳንድ አካባቢዎች የሚታዩ የጊዜያዊ ምርጫ ውጤቶች አዲስ በሚመሰረተው የክልልም ሆነ የተወካዮች ም/ቤቶች አዳዲስ ድምፅ የሚሰማባቸው ሁኔታዎች እንዲሚኖር ጠቋሚ መሆናቸው ተባለ። ምክር ቤቶች የተለያዩ ፓርቲዎች ድምጾችን ካስተናገዱ ጠንካራ አገራዊ መመሪያ እና ስልታዊ በውይይት ዳብሮ እንዲወጣ ያደርጋል ሲሉ የፖለቲካ ምሁር ተናግረዋል። 

https://p.dw.com/p/3vR45
Äthiopien Wähler betrachten Wahlergebnisse in Bahirdar
ምስል Alemnew Mekonnen/DW

«የጊዜያዊው የምርጫ ውጤት»

6ኛው አገራዊ ምርጫ በብዙ ሂደቶች አልፎ ፣ የተቆረጠለት የምርጫ ቀን ሁለት ጊዜ ተራዝሞና በአንዳንድ አካባቢዎች በተለያዩ ምክንያቶች አሁንም የምርጫ ጊዜው ሌላ ጊዜ ተቀጥሮለት ባለፈው ሰኞ ምርጫ በሚካሄድባቸው አካባቢዎች ተካሂዶ በአብዛኛው ሰላማዊ በሆነ መንገድ ተጠናቅቋል። ብዙዎቹ እንደሚያምኑት ምርጫው ከዚህ በፊት ከተደረጉ ምርጫዎች አንፃር ሲታይ በሁሉም መልኩ ሰላማዊና ነፃ ነበር፣ በዚህ ምክንትም ያልተገመቱ ውጤቶችም በጊዜያዊነት እየወጡ እንደሆነ የባህር ዳር ከተማ ነዋሪዎች አመልክተዋል፡፡ ምርጫው ከተካሄደ በኋላ የወጡ ጊዜያዊ የምርጫ ውጤቶች በክልልና በፌደራል ተወካዮች ምክር ቤቶች የተለያዩ ድምፆች የሚሰሙበት ሁኔታ እንደሚኖርም ነዋሪዎች ተናግረዋል፡፡ በባሕር ዳር ዩኒቨርሲቲ የፖለቲካል ሳይንስና ዓለም አቀፍ ግንኙነት መምህር ቻላቸው ታረቀኝም የሚመሰረቱ ምክር ቤቶች ብዝሐ ድምፅ ሊስተናግዱ የሚችሉበት አዝማሚያ እንደሚታይ አስረድተዋል፡፡ አዳዲስ ድምፆች ወደ ክልልም ሆነ ተወካዮች ምክር ቤቶች መግባት ከቻሉ በክርክርና በውይይት የዳበሩ ጠንካራና ገንቢ ፖሊሲዎችንና ህጎችን ለማውጣት ጠቃሚ ሆናልም ብለዋል፡፡ አቶ ቻላቸው እንደሚሉት በምክር ቤቶች የብዝሐ ድምፅ መኖር አዳዲስ ፖሊሲዎችን አጠንክሮ ከማውጣት ባለፈም ቀደም ሲል እንከን የነበረባቸውን ለመከለስም እድል ይፈጠራል፡፡ ከ100 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ባለባት ኢትዮጵያ፣ ከ37 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ለስድስተኛው አገራዊ ምርጫ በመራጭነት ተመዝግቦ እንደነበር ይታወሳል፡፡

ዓለምነው መኮንን

ሸዋዬ ለገሠ

ኂሩት መለሰ