1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በትግራይ ክልል 10 ከተሞች ሰላማዊ ሰልፎች ተካሄዱ

እሑድ፣ ኅዳር 16 2011

በትግራይ ክልል 10 ከተሞች ዛሬ ሰላማዊ ሰልፎች ተካሄዱ። ሰልፈኞቹ “ፍትህ ለሁሉም፣ ህገ መንግስቱ ይከበር” የሚሉ ጥያቄዎችን በዋነኛነት አንግበው እንደነበር ተነግሯል፡፡ ከሰልፉ ጋር በተያያዘ ትላንት ምሽት በአላማጣ ከተማ ሶስት ቦምቦች ቢፈነዱም ምንም ዓይነት ጉዳት አለማድረሳቸውን ደግሞ የከተማው ከንቲባ ለDW ገልጸዋል።

https://p.dw.com/p/38smd
12.06.2013 DW Online Karten Basis Äthiopien Englisch

በትግራይ ክልል 10 ከተሞች ሰላማዊ ሰልፎች ተካሄዱ

ዛሬ በትግራይ ክልል በክልሉ በማዕከላዊ እና ደቡብ ዞኖች ባሉ ከተሞች የተደረጉት ሰልፎች በዋነኝነት ብሔርን መሰረት ያደረጉ ጥቃቶችን የሚያወግዙ ነበሩ፡፡ የሰልፉ ተሳታፊዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ የሕግ የበላይነት መሸርሸሩን በመጥቀስ መንግስት መፍትሄ ሊያበጅለት ይገባል ብለዋል፡፡ አክሱም፣ ዓድዋ፣ ሑመራ፣ ዓብይዓዲ፣ መኾኒ፣ አላማጣ፣ ኮረምና ሌሎች ከተማች ዛሬ ሰልፍ ካስተናገዱ መካከል ናቸው፡፡

ከሰልፉ ጋር በተያያዘ ትላንት አላማጣ ከተማ ውጥረት ሰፍኖባት ውላለች፡፡ ትላንት ቅዳሜ ማታ ሶስት ሰዓት ገደማ በከተማዋ ባለ ኢትዮጵያ ሆቴል አካባቢ በተመሳሳይ ጊዜ 3 ቦምቦች መፈንዳታቸውን ምንጮች ገልፀውልናል፡፡ በፍንዳታው በሰው ሕይወት ላይ የደረሰ ጉዳት አለመኖሩን የአላማጣ ከተማ ከንቲባ አቶ ሀፍቶም ወሬታ ለDW ተናግረዋል፡፡ 

ከቦምብ ፍንዳታዎች አስቀድሞ በከተማዋ የተለያዩ ያልተለመዱ እንቅስቃሴዎች ሲደረጉ መዋላቸውም ተነግሯል፡፡ "የቦምብ ጥቃት ሙከራው ህዝብ በሰልፉ ላይ እንዳይሳተፍ ጫና ለመፍጠር ነበር" ብለዋል ከንቲባው አቶ ሀፍቶም፡፡

ዛሬ በተለያዩ የትግራይ ክልል ከተሞች በተመሳሳይ ሰዓት በተደረጉ ሰልፎች "ፍትህ ለሁሉም" ፣ "ሕገ መንግስት ይከበር" ፣ "የትግራይ ህዝብን ለማንበርከክ የሚደረግ ማንኛውንም እንቅስቃሴ አንቀበልም" ፣ "ተጠርጣሪዎች በሌላ አካል መዳኘት የለባቸውም" የሚሉ መፈክሮችን ሰልፈኞቹ አሰምተዋል፡፡

ሙሉ ዘገባውን ለማድመጥ የድምጽ ማዕቀፉን ይጫኑ።

ሚሊዮን ኃይለስላሴ

ተስፋለም ወልደየስ