1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በትግራይ የነዳጅ እጥረት

ረቡዕ፣ ሰኔ 29 2014

በነዳጅ እጦት ምክንያት በትግራይ የትራንስፖርት አገልግሎት ተቋርጧል አልያም ተወዷል።የዓለምአቀፍ ተቋማት እርዳታ ጭምር በክልሉ ወደ ተለያዩ አካባቢዎች ማዳረስ እንዳልተቻለ የትግራይ ክልላዊ መንግስት ይገልጻል።ካለፈው ዓመት ሰኔ ወዲህ በመደበኛነት ትግራይ የገባ ነዳጅ የለም።81 ነዳጅ ማደያ ድርጅቶች ከዓመት በላይ ለሚሆን ግዜ ከስራ ውጭ ሆነዋል።

https://p.dw.com/p/4DlX9
Äthiopien Auswirkungen des Brennstoffmangels in der Region Tigray
ምስል Million Hailesilassie/DW

በትግራይ የነዳጅ እጥረት ያሳደረው ተጽእኖ

በትግራይ በነዳጅ አቅርቦት እጦት ምክንያት የህዝብ አገልግሎቶች እና እንቅስቃሴ መስተጓጎሉ ተገለፀ። የክልሉ መንግስት እንደሚለው በነዳጅ አቅርቦት እጦት ምክንያት በዓለምአቀፍ ተቋማት ወደ ትግራይ የገባ የምግብና መድሃኒት እርዳታ፥ ከመቐለ መጋዝኖች ወደ ተለያዩ የትግራይ አካባቢዎች አጓጉዞ ለተቸገረዉ ህዝብ ማዳረስ አልተቻለም። የነዳጅ እጦቱ የሕክምና ተቋማትን ስራም ማደናቀፉ ተገልጿል። በነዳጅ እጦት ምክንያት በትግራይ የህዝብ ትራንስፖርት ዋጋ ከ400 እስከ 500 በመቶ መጨመሩን ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ ከመቀሌ ዘግቧል።

የትግራይ የአደጋዎች ቅድመ ጥንቃቄ እና ምላሽ ዳይሬክቶሬት እንደሚገልፀው በነዳጅ አቅርቦት እጦት ምክንያት በዓለምአቀፍ ለጋሽ ድርጅቶች ወደ ትግራይ የገባ የምግብና መድኃኒት ድጋፎች ከመቐለ መጋዝኖች ወደ ተለያዩ የትግራይ አካባቢዎች አጓጉዞ አደጋ ላይ ለወደቀ ህዝብ ማዳረስ አልተቻለም። የተቋሙ ዳይሬክተር አቶ ገብረእግዚአብሔር አረጋዊ ለዶቼቬለ እንዳሉት "ከእያንዳንዱ የዕርዳታ ኮንቫይ ጋር ለስርጭት የሚረዳ በቂ ነዳጅ ሊገባ ነበር የሚጠበቀው። ሆን ተብሎ ነዳጅ እንዳይገባ ክልከላ ተደርጎ ስላለ እርዳታ ወደ ህዝብ ማዳረስ አልተቻለም። 

Äthiopien Auswirkungen des Brennstoffmangels in der Region Tigray
ምስል Million Hailesilassie/DW

የነዳጅ አቅርቦት እጦቱ በትግራይ የሚገኙ የሕክምና ተቋማት ስራንም ያደናቀፈ ሆንዋል። ከጤና ጣብያ እስከ ሪፈራል ሆስፒታል ደረጃ ያሉ የሕክምና ተቋማት ነዳጅ ባለማግኘታቸው የአምቡላንስ አገልግሎት አቋርጠዋል፣ አማራጭ ሀይል የሚያገኙበት ስርዓት ተስተጓጉሏል። በትግራይ ትልቁ የሕክምና ተቋማ ዓይደር ሪፈራል ሆስፒታል በነዳጅ እጦት የአምቡላንስ አገልግሎት ካቋረጠ ወራት አልፈዋል።

በነዳጅ እጦት ምክንያት በትግራይ የትራንስፖርት ዋጋ ከነበረው ከ400 እስከ 500 በመቶ የጨመረ  ሲሆን፣ በኮንትሮባንድ ነጋዴዎች የገባ የተባለ ቤንዚን እና ናፍታ በሊትር እስከ 400 ብር በጎዳናዎች ይሸጣል። ለትራንስፖርት ችግሩ እንደመፍትሄ የሚመስል ለዓመታት ጠፍተው የነበሩ በእንስሳት ጉልበት የሚሰሩ ጋሪዎች አሁን አሁን በመቐለ ጎዳናዎች የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት እየሰጡ መመልከት የተለመደ ሆንዋል።

ሚሊዮን ኃይለ ሥላሴ

ኂሩት መለሰ

ማንተጋፍቶት ስለሺ