1. ወደ ይዘቱ ዝለል
  2. ወደ ዋናዉ ገፅ ዝለል
  3. ወደ ተጨማሪ የDW ድረ-ገፅ ዝለል

በትግራይ ክልል አስራ አራት ሰዎች በረሐብ መሞታቸውን ባለሥልጣናቱ ተናገሩ

እሑድ፣ ነሐሴ 30 2013

በኢትዮጵያ መንግሥት እውቅና የተነፈገው የትግራይመስተዳድር የግብርና እና ገጠር ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አትንኩት መዝገቡ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ሽሬ አካባቢ ዘጠኝ ሰዎች እንዲሁም በክልሉ ማዕከላዊ ዞን አምስት ሰዎች በረሐብ ምክንያት መሞታቸውን ተናግረዋል።

https://p.dw.com/p/3zv5C
Tigray Konflikt | Äthiopien Eritrea Flüchtlinge
ምስል YASUYOSHI CHIBA/AFP

በትግራይ ክልል በረሐብ ምክንያት አስራ አራት ሰዎች መሞታቸውን ባለሥልጣናት ተናገሩ። በኢትዮጵያ መንግሥት እውቅና የተነፈገው የትግራይ ክልላዊ መንግሥት የግብርና እና ገጠር ልማት ቢሮ ኃላፊ ዶክተር አትንኩት መዝገቡ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ ሽሬ አካባቢ ዘጠኝ ሰዎች እንዲሁም በክልሉ ማዕከላዊ ዞን አምስት ሰዎች መሞታቸውን ተናግረዋል።

ኃላፊው በክልሉ ለተረጂዎች መድረስ የነበረበት ዕርዳታ እየቀረበ እንዳልሆነ ተናግረው የኢትዮጵያን መንግሥት ወቅሰዋል።

በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ዕርዳታ ጊዜያዊ አስተባባሪ ግራንት ሌይቲ ከትናንት በስቲያ ሐሙስ ባወጡት መግለጫ የነፍስ አድን ዕርዳታ ወደ ክልሉ ማጓጓዝ እንዳልተቻለ አስታውቀው ነበር።

ዶይቼ ቬለ በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ የቀረቡ ክሶች ላይ ከሰላም ሚኒስቴር እና የብሄራዊ የአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ባለሥልጣናት ማብራሪያ ለመጠየቅ ያደረገው ጥረት አልተሳካም።

የሰላም ሚኒስቴር ዛሬ ቅዳሜ ባወጣው መግለጫ ምግብ እና ምግብ ነክ ዕርዳታ፣ የተሻሻሉ ምርጥ ዘሮች እና ማዳበሪያ የጫኑ 500 ተሽከርካሪዎች ወደ ትግራይ መጓዛቸውን አስታውቋል። በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ መግለጫ መሠረት ከእነዚህ መካከል 152 ተሽከርካሪዎች ወደ ትግራይ ያቀኑት ባለፉት ሁለት ቀናት ነው።

ሚሊዮን ኃይለስላሴ

እሸቴ በቀለ